አሻራ ለመስጠት ያለ እንግልትን እና የሚጠየቅ ሙስናን በተመለከተ መሠረት ሚድያ በቅርቡ የሰራውን የምርመራ ዘገባ ተከትሎ ለውጥ መደረጉን ፌደራል ፖሊስ ዛሬ አስታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- ሚድያችን ሚያዝያ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ወደ መካከለኛው ምስራቅ አገራት ለስራ ለሚሄዱ ኢትዮጵያውያን ዜጎች የአሻራ ምርመራ ወይም የወንጀል ነፃ ሰርተፍኬት አሰጣጥ ላይ ያለውን እጅግ አሰልቺ እንግልት እና ለአላስፈላጊ ወጪ የሚዳርግ ቢሮክራሲ በማጋለጥ ያቀረበው ዝርዝር የምርመራ ዘገባን ተከትሎ ፌደራል ፖሊስ ዛሬ ለውጥ መደረጉን ገልጿል።
ይህ ዘገባ ይፋ ከሆነ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ዛሬ ባወጣው ይፋዊ መግለጫ ተገልጋዮች የወንጀል ነፃ ሰርተፍኬት ለማውጣት ካሉበት የኢትዮጵያ ክፍል ሁሉ ተጉዘው አዲስ አበባ በሚገኘው የፎረንሲክ ምርመራ ዳይሬክቶሬት በአካል መገኘት የነበረባቸውን አስገዳጅ አሰራር መቀየሩን በግልጽ አስታውቋል።
ከግንቦት 06 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ በሚሆነው በዚህ አዲስ መመሪያ መሰረት ተገልጋዮች በአካል አዲስ አበባ መምጣት ሳያስፈልጋቸው በስራና ክህሎት ሚኒስቴር በተዘጋጁ ማዕከላት አማካኝነት በየአካባቢያቸው በሚገኙና በሚልኳቸው ህጋዊ ኤጀንሲዎች በኩል አገልግሎቱን በቀላሉ ማግኘት እንደሚችሉ ፖሊስ ገልጿል።
መሠረት ሚዲያ በዘገባው ዜጎች ለቀናት በፀሀይ እና በዝናብ በመንከራተት እንዲሁም ለአላስፈላጊ የትራንስፖርት እና የሆቴል ወጪዎች እየተዳረጉ ይፈጸምባቸው የነበረውን እንግልት በማስረጃ አስደግፎ ማቅረቡ ለፌዴራል ፖሊስ ውሳኔ እንደ ዋና ግብዓት እና መነሻ ሆኖ እንዳገለ ታውቋል።
"የምንከፍለውን ዋጋ ለህግ አድርሱልን" ያሉ በርካታ ሰዎች ለሚድያችን በፅሁፍ እና በድምፅ ያደረሱት መረጃ እንደሚያሳየው ከሳምንታት በፊት በፌደራል ፖሊስ አሻራ ለመስጠት እስከ 5 እና አልፎ አልፎም አንድ ሳምንት ደጃፍ ተሰልፎ መጠበቅ ግድ ሆኖ ነበር።
"ይሄው ዛሬ አምስተኛ ቀናችን ነው፣ ቀንም ሌትም ከዛው ነው አዳራችን። እሱን ብንችለውም የፖሊስ ዱላ እና ድብደባ መቋቋም አልቻልንም፣ በዛላይ በተደራጁ ሌባዎች ዝርፊያው ለጉድ ነው" በማለት በወቅቱ የተናገሩት አንድ ተስተናጋጅ ናቸው።
አክለውም "ምንም መፍትሄ እያገኘን አይደለም፣ እኛ ከዛው ተሰልፈን ውለን አድረን አንዳንዶች በአቋራጭ እስከ 10 ሺህ ብር እየከፈሉ ያስጨርሳሉ" በማለት አስረስተዋል።
ሌላ ወጣት ደግሞ እናስጨርስላችኋለን ብር ክፈሉ ተብለው የከፈሉ ይካዳሉ፣ ይህም ብዙዎችም ተስፋ እያስቆረጠ ነው በማለት አስረድቶ ነበር።
"አይን ቢያይ ተስፋ መቁረጥ ብቻ ሳይሆን በሚሆነው ነገር ታዝናለህ፣ የት ሂደን ጉዳያችን ይታይ? ለማን እንጩህ? በየመን በረሀ ህይወታችን ከሚያልፍ በህጋዊ መንገድ ለመሄድ ነበር ፣ ነገር ግን ተስፋ ቆረጥን። እውነት ግን ለመንግስት የኢትዮጵያ ወጣት የቀይ ባህር የአዞ እራት መሆን ለሀገር ኩራት ነው ወይ?" ብሎ ይጠይቃል።
ሚድያችን የደረሰው ተደጋጋሚ መረጃ እንደሚጠቁመው ለውጭ ሀገር የስራ ጉዞ በፌደራል ፖሊስ የአሻራ መስጫ ቢሮ በቀን እስከ 5 ሺህ ሰዎች ተሰልፈው ሲጠብቁ ነበር።
| መሠረት ሚድያ |


