የፈረንሳይ ኤምባሲ በጋዜጠኛ ኦገስቲን ፓሲሊ መባረር ዙሪያ ከኢትዮጵያ ሚዲያ ባለስልጣን ማብራሪያ እየጠበቀ መሆኑን ለመሠረት ሚድያ ገለጸ
(መሠረት ሚድያ)- በኢትዮጵያ የሚገኘው የፈረንሳይ ኤምባሲ ፈረንሳዊቷ ፍሪላንስ ጋዜጠኛ ኦገስቲን ፓሲሊ ከሀገር እንድትባረር የተደረገበትን ምክንያት በተመለከተ ከኢትዮጵያ ሚዲያ ባለስልጣን ማብራሪያ ለመጠየቅ ጥረት ቢያደርግም እስካሁን ምላሽ እንዳላገኘ አስታውቋል።
ኤምባሲው ለመሠረት ሚዲያ በሰጠው ምላሽ የጋዜጠኛ ኦገስቲንን ሁኔታ በተመለከተ ከኢትዮጵያ ሚዲያ ባለስልጣን ጋር ለመገናኘት ጥያቄ አቅርቦ እንደነበር ገልጿል።
ነገር ግን በተደጋጋሚ ሙከራዎች ቢደረጉም ኤምባሲው ጋዜጠኛዋ ከተባረረችበት ምክንያት ጀርባ ስላለው ዝርዝር ጉዳይ እስካሁን ምላሽ ወይም ማብራሪያ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኝ በይፋ አስታውቋል።
ለፈረንሳዩ ታዋቂ የዜና አውታር “ላ ክሯ” እና ለሌሎች ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በኢትዮጵያ ቆይታዋ ሰብአዊ ጉዳዮችን፣ የሱዳን ስደተኞችን ሁኔታ እና ማህበራዊ ቀውሶችን ስትዘግብ የነበረችው ፍሪላንስ ጋዜጠኛ ኦገስቲን ፓሲሊ ከሁለት ቀናት በፊት ከኢትዮጵያ መባረሯ ታውቋል።
ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጋዜጠኛዋን ያባረሩበትን ዝርዝር ምክንያት እስካሁን በይፋ የገለጹት ነገር የለም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (CPJ) የኢትዮጵያ ባለስልጣናት የጋዜጠኛዋን የመኖሪያ ፍቃድ እና የሚዲያ ዕውቅና በአስቸኳይ እንዲመልሱና ወደ ሀገር ውስጥ ገብታ ስራዋን እንድትቀጥል እንዲፈቅዱላት ጠይቋል።
የድርጅቱ የአፍሪካ ዳይሬክተር አንጄል ኩንታል እንደገለጹት ጋዜጠኛዋ የተባረረችው በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ተገኝታ ነዋሪዎች ወደ ጦርነት ልንመለስ እንችላለን በሚል ስላላቸው ስጋት የሰራችውን ዘገባ ተከትሎ የተወሰደ የበቀል እርምጃ ነው።
ባለስልጣናት በይፋ መወያየትና መፈተሽ የማይፈልጉትን የፖለቲካ እና የፀጥታ ጉዳይ በገለልተኝነት የዘገበችን ጋዜጠኛ በቁጥጥር ስልጣናቸው ተጠቅመው መቅጣታቸው ተገቢ እንዳልሆነ ድርጅቱ ገልጿል።
የኦገስቲን ፓሲሊ ከሀገር መባረር በሀገሪቱ ውስጥ ገለልተኛ በሆኑ የሀገር ውስጥና የአገር ውጭ መገናኛ ብዙሃን እና ጋዜጠኞች ላይ እየተወሰደ ካለው ተከታታይ እና ጠንካራ እርምጃ ጋር የተያያዘ መሆኑ ይነገራል። በድንበር የለሽ የጋዜጠኞች ቡድን የዓለም የፕሬስ ነፃነት መውጫ ጠቋሚ መሠረት የኢትዮጵያ ደረጃ በከፍተኛ ሁኔታ በማሽቆልቆል ላይ ይገኛል።
በተለይም በቅርብ ዓመታት በሀገሪቱ ከተቀሰቀሱት የውስጥ ግጭቶች የአንዳንዶቹ መጠናቀቅና አዳዲስ አለመረጋጋቶች መፈጠር ማግስት መንግስት መረጃዎችን ለመቆጣጠር የሚያደርገው ጥረት መጨመሩን እና የሚዲያ ምህዳሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠበበ መምጣቱን የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅቶች በተደጋጋሚ በማሳሰብ ላይ ናቸው።
| መሠረት ሚድያ |


