በጀነራል ሰአረ መኮንን ግድያ የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት የነበረው ግለሰብ ከእስር ቤት ውስጥ ተወስዶ አሁን ያለበት ቦታ አለመታወቁ ተገለጸ
(መሠረት ሚድያ)- ከሰባት አመት በፊት የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም የነበሩትን ጀነራል ሰአረ መኮንን እና ሜጀር ጀነራል ገዛኢ አበራን በመግደል ወንጀል ጥፋተኛ ተብሎ የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት የነበረው አስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ ከታሰረበት አባ ሳሙኤል ማረሚያ ቤት በትናንትናው ዕለት ተወስዶ ያለበት ቦታ አለመታወቁ ተገለጠ።
የመንግስት የመረጃ ምንጮች ለመሠረት ሚድያ እንደተናገሩት የጥበቃ አካላት ተከሳሹን ዞን 22 ተብሎ ከሚጠራው የማረሚያ ቤቱ ክፍል ወስደውት የሄዱ ሲሆን ለምን ዓላማ እና ወዴት እንደወሰዱት እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።
የማረሚያ ቤቱ አንድ ባልደረባም አስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ ትናንት ከእስር ቤቱ ተወስዶ መሄዱን እና እስካሁንም ያለበት ሁኔታ እንደማይታወቅ አረጋግጠዋል።
አስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ የጀነራል ሰአረ መኮንን የቅርብ የጥበቃ አባል የነበረ ሲሆን በወቅቱ በአማራ ክልል ከተካሄደውና ከከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ ከተማ በተፈጸመው ጥቃት ዋና ተጠርጣሪ ሆኖ በቁጥጥር ስር መዋሉ ይታወሳል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ የሕገ መንግሥት እና የፀረ ሽብር ችሎት በግድያ ወንጀሉ ጥፋተኛ ብሎ በመፍረድ የእድሜ ልክ ፅኑ እስራት ፈርዶበት እንደነበር የፍርድ ቤት መዝገቦች ያሳያሉ።
በወቅቱ ዓቃቤ ሕግ ተከሳሹ የተጣለበትን የሕዝብና የመንግሥት አደራ በመጣስ እንዲሁም ወንጀሉን ለማቀናጀትና ለመፈጸም በማሴሩ ምክንያት የሞት ቅጣት እንዲጣልበት ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ነበር። በሌላ በኩል የተከሳሹ የሕግ ጠበቆች ደንበኛቸው ከዚህ ቀደም ምንም ዓይነት የወንጀል ሬኮርድ የሌለው መሆኑን በመጥቀስ የሞት ቅጣት መጣሉ ሕገወጥ ነው ሲሉ ተከራክረው ነበር።
ፍርድ ቤቱም የቀረቡትን ማቅለያዎች እና ማክበጃዎች መዝኖ በመጨረሻም አስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ በእድሜ ልክ እስራት እንዲቀጣ ውሳኔ አስተላልፎ ወደ አባ ሳሙኤል ማረሚያ ቤት እንዲላክ አድርጎ ነበር።
አሁን ላይ ተከሳሹ በፅኑ እስራት ላይ እያለ ድንገት ከማረሚያ ቤቱ ተወስዶ ያለበት ቦታ አለመታወቁ በጉዳዩ ተከታታዮች ዘንድ ጥያቄን ፈጥሯል።
የፀጥታ አካላት ተከሳሹን ለምን እንደወሰዱት እና አሁን የት እንደሚገኝ እስካሁን ከየማረሚያ ቤቱ ወይም ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ የለም።
| መሠረት ሚድያ |


