ግሽበት ቀንሷል? የመንግሥት ብድርስ?
(መሠረት ሚድያ)- የመንግሥት ብድር በ12 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ዜሮ ሆኗል፣ ግሽበትም ቀንሷል ይላሉ የብሔራዊ ባንክ ገዢ አቶ ማሞ እስመላለም ምኅረቱ። የመንግሥት ብድር ሲባል ከብሔራዊ ባንክ የተበደረው ብድር እንደማለት ነው እንጂ የውጭ ዕዳ ማለት አይደለም፣ የውጭ ዕዳ የ IMF አዲሱ ብድር ሳይጨምር $28 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሲኖርብን ከዚህ ውስጥ ግማሹ የቻይና እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ።
የሀገር ውስጥ ዕዳን እንደ ዕዳ መቁጠር የትራዲሽናል ማለትም የዩኒቨርሲቲ መደበኛ ፋይናንስና ኢኮኖሚክስ አረዳድ ነው:: መንግሥት ከብሔራዊ ባንክ አልተበደረም ማለት ምን ማለት ነው? ትንሽ ከፍ እናድርገውና አሜሪካ ዶላር አልፈጠረችም እንደማለት ነው:: እዚህ ጋር በጥንቃቄ ተረዱት:: አሜሪካ ኢኮኖሚዋን የምታንቀሳቅሰው አዳዲስ ዶላር በመፍጠር ነው:: በኮቪድ 19 ወቅት በአንድ ዓመት ብቻ ከ$13 ትሪሊዮን ዶላር በላይ ፈጥራለች:: ዶላር ትፈጥርና ከዓለም ሀገራት ንብረት ትወስዳለች:: ይህንን ብትተው ወዲያው ትወድቃለች:: የአሜሪካ ትልቁ ኤክስፖርት ግሽበት ነው:: አሜሪካ ብድር አትፈራም:: ወረቀት አውጥታ ወርቅ ትቀበላለች እንጂ ዶላር የራሷ ስለሆነ ምንም አይሠራላትም::
ይህንን ወደ ኢትዮጵያ መንግሥት ብናመጣው መንግሥት ከብሔራዊ ባንክ አልተበደረም ማለት ኢኮኖሚውን የሚያንቀሳቅሰው በታክስ ነው ማለት ነው:: ታክስ ማለት ከሕዝብ ላይ ወርቅ ሳይሆን ባዶ ቁጥር መሰብሰብ ነው:: በአናቱም ከዝውውር (circulations) ላይ ብር በታክስ መልክ ሲሰበስብ የሥራ እንቅስቃሴን ይገድላል:: ብር በራሱ የሚዳሰስ, የሚታይ, የሚቀመስ, የሚቆጠር አይደለም:: ከአየር የቀጠነ የመንግሥት ፍላጎት ነው:: ይህ ፍላጎት ወይም አዋጅ የመግዛት ኃይልን ይፈጥራል:: መንግሥት ብርን መፍጠር ካልቻለ ኃይል የለውም ማለት ነው::
መንግሥት ከብሔራዊ ባንክ ሲበደር ግን ወርቆችን መሰብሰብ ይችላል:: በድንበሮች Smuggled የሚሆንን ወርቅና ከብት ወደ ማዕከላዊ መንግሥት ይመጣል:: ምክንያቱም መንግሥት በፈለገው ዋጋ መግዛት ይችላል:: ወደ ውጭ ይፈልስ የነበረ ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ የመጣው በዚህ ስልት ነው:: የዓለም ሁሉ ወርቅና ጨርቅ, ምሁርና ምርት ወደ አሜሪካ የሚሄደው በዚሁ የመግዛት ኃይል እንደሆነ በመደበኛ (ትራዲሽናል) ትምህርት ላናገኘው እንችላለን::
መንግሥት ከብሔራዊ ባንክ መበደር ትቶ ከዝውውር ላይ ሲሰበስብ ምርት ይቀንስና ግሽበት ይጦዛል:: ለምን? ሠራተኛ መንቀሳቀሻ ስለሚያጣ:: ግሽበት የቀነሰ የሚመስለን የምር ቀንሶ ሳይሆን እንቅስቃሴና ፍጆታ (consumption) በመቀነሱ ነው:: አብዛኛው የሀገራችን ክፍል ሰላም ባለመሆኑ እንቅስቃሴ የለም በሚያስብል ደረጃ ነው ያለው:: ኤርትራን ብንወስድ ግሽበት የሌለ የሚመስለን እንቅስቃሴ እጅግ ደካማ በመሆኑ ነው:: ወጥቶ መግባት ቅንጦት በሆነበትና ትንሽ ብር በባንክ ማሳደር የሽፍታና አጋች ሲሳይ በሚያደርግበት የኢትዮጵያ ከባቢ (environment) ግሽበት ቀንሷል ማለት አይቻልም::
መንግሥትም ከብሔራዊ ባንክ አልተበደረም ማለት ሥራ ትቶ "ቀፋይ" ሆኗል ማለት ነው:: (ትራዲሽናል ኢኮኖሚስት ተረጋጉ):: መንግሥት የሆነ ብር ሲያይ "ያዙት እሰሩት" ካለ ወይም ካሳደደ ማለት 99 ቆነጃጅት ሚስቶች እያሉት በመልክም በጸባይም ያልታደለችን ፍለጋ ጫካ ለጫካ እንደመሯሯጥ ነው:: ምክንያቱም እጁ ላይ ያለን ምንጭ ትቶ ሥራና ሠራተኛን ይቀጣል::
መንግሥት ትኩረቱ ሥራ ፈጠራ ላይ ሳይሆን ቁጥርን የማሳደድ ቁጥጥር ላይ ይሆናል:: ግሽበት የሚፈጠረው ብዙ ብር በመፍጠር ብቻ ይመስለናል:: በርግጥ ይፈጥራል:: ምንም ጥርጥር የለውም:: የግሽበቶች ዋነኛው ምንጭ ግን አለመሥራት ነው:: የምንዛሪ ምንጩ ላብ እንጂ ቁጥጥር አይደለም:: ዶላር ባዶ ቁጥር ነውና:: ብዙ አምርተን ብዙ ስንልክ ነው ምንዛሪ የምናመነጨው::
በሀኪሞቹ የተጀመረው እንቅስቃሴ የዚህ ውጤት ነው:: የመቶ ሺህ ለፍቶ አስር ሺህ ብር ሰጥተኸው ሰባት ሺህ ብር ስትወስድበት መቋቋም አይችልም:: ወደ ፋብሪካም ብንወስደው ይኸው ነው:: ብዙ ይለፋል:: ግን በሰላቢ ይሰለባል:: ኃይሉ በታክስና በጉቦ ያልቃል:: የሚለፋው ለምንዛሪ ሳይሆን ለመዝባሪ ይሆናል::
ያደጉ የምንላቸው ሀገራት ጎብኙ:: እድገታቸው ታክስን ጨምሮ እንቅፋት የተባለን ሁሉ በማስወገድ ነው:: የአሜሪካ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ለእኛ ከማይሠራበት ትልቁ ነጥብ እኛ የምንሠራው ለውጭ ምንዛሪ ሲሆን አሜሪካውያን ስለ ውጭ ምንዛሪ አያውቁም:: ቢያውቁም አይጨነቁም::
ይህንን ልዩነት የምንፈታው ቻይና በፈታችበት መንገድ ነው:: ብር የማይቸግረው ጠንካራና ማዕከላዊ መንግሥት አቋቁመን ኢኮኖሚውን ግን ሊበራል ማድረግ ነው:: አሜሪካ ዶላርን ስታትም ቻይና በአላቂ (Consumables) ትሰበስበውና ያው ዶላር ባዶ ቁጥር ወይም ወይም ወረቀት ስለሆነ ጥሬ ዕቃ በመግዛት ታስወግደዋለች::
ላባደር ሲሠራ በፍጹም ታክስን ማሰብ የለበትም:: ምክንያቱም ሥራን ይገድላል:: ታክስ ከጣልንም ቀድሞ የሚሰበሰብ ቁርጥ ታክስ ሆኖ ላባደሩ በሠራው ልክ ማግኘትና መንግሥት ደግሞ የሆነ ሴክተር ወይም መልክዓምድር ላይ ክፍተት ሲያይ አጠገቡ ካለው ካዝና እየዘገነ ማሽንና ግብአት እያቀረበ ያሟላዋል:: ምክንያቱም የብር ችግር የለበትም:: ሲበዛም ብሩን ሰብስቦ ማቃጠል ይችላል:: ማቃጠልም አያስፈልግም:: በጀቱን ማቃጠል ወይም ማጠፍ በቂ ነው::
በዚህ ልክ ቀላል የሆነን ነገር አወሳስበን ተወሳሰበብን:: ያለ ዕድሜ በዲፕረሽን ሸበትን::
እራሱ በነጻ የሚያወጣውን ብር ሠራተኛውን እያስለቀሰ መሰብሰብ ግሽበትን ማባባስና ውድቀትን ማፍጠን እንጂ ኢኮኖሚያችንን አያሻሽልም::
(ብዙ ደረሰኝ መቁረጥ እንዴት ብዙ ዛፍ መቁረጥ እንደሆነ እመለስበታለሁ:: ስላዳመጣችሁኝ አመሰግናለሁ)::
አብዱልቃድር ሀጅ ኑረዲን
መረጃን ከመሠረት!




Finally I got it
ፋይናንስን የሚመራው አካልና መንግስት የዋጋ ግሽበትን የተረዱበት መንገድ በጣም የተሳሳተ ነው። ይህን ዘገባ ከልብ ቢመለከቱት በጣም ቆንጆ ነው።