የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ገቢ ማመንጫ ኢንተርፕራይዝ ሰራተኞች ስራ የማቆም እርምጃ ሊወስዱ ነው
(መሠረት ሚድያ)- የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ገቢ ማመንጫ ኢንተርፕራይዝ ሰራተኞች ለረጅም አመታት ሲጠይቁ የነበረው የደሞዝ ማሻሻያ ጥያቄ ምላሽ ባለማግኘቱ በአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ 1156/2011 አንቀፅ 160(2) መሰረት ህጋዊ ስራ የማቆም እርምጃ ሊወስዱ መሆናቸው የደረሰን መረጃ ይጠቁማል።
ኢንተርፕራይዙ የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የገቢ ማስገኛ ድርጅቶችን ለማቋቋም ባወጣው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደምብ በመቋቋም የተለያዩ የንግድ እና ገቢ ማስገኛ ስራዎችን ሲሰራ የቆየ ነው።
ይሁንና የኢንተርፕራይዙ ሰራተኞች ከ2008 ዓ/ም ጀምሮ አንድም ግዜ የደሞዝ ጭማሬ እንዳልተደረገላቸው ለመሠረት ሚድያ ተናግረዋል።
"ከቅርብ አመታት ወዲህ እንደ ሀገር እየገጠመ ከመጣው ከፍተኛ የኑሮ ውድነት እና የዋጋ ግሽበት ምክንያት ስራችንን ተረጋግተን መስራት እንዳንችል አድርጎናል" የሚሉት ሰራተኞቹ በዘንድሮው አመት ሁለት ግዜ ደሞዝ እንዲጨመርላቸው ቢጠይቁም አጥጋቢ ምላሽ እንዳላገኙ ይናገራሉ።
"ላለፉት ዘጠኝ አመታት የደሞዝ ማሻሻያ ሳይደረግልን እየሰራን ለምንገኝ ሰራተኞች ለተጠየቀው መሰረታዊ የመኖር እና አለመኖር የህልውና ጥያቄ ትኩረት በመስጠት በቂ ምላሽ ባለመመለሱ ምክንያት ጉዳዩን ለዩኒቨርስቲው ፕሬዝደንት አቅርበዋል፣ እርሳቸውም ምላሽ ነፍገውናል" በማለት የገጠማቸውን አብራርተዋል።
ይህን ተከትሎም ሰራተኞቹ ከሳምንት በፊት የ10 ቀን ምላሽ መስጫ ለዩኒቨርስተው ሰጥተው የነበረ ቢሆንም እስካሁን ምላሽ ስላላገኙ የስራ ማቆም እርምጃ ሊወስዱ እየተዘጋጁ መሆኑ ታውቋል።
"ለሚፈጠረው ችግር ሀላፊነቱን አንወስድም" ያሉት ሰራተኞች የስም ዝርዝራቸውን ለዩኒቨርስቲው ማስገባታቸውን የደረሰን መረጃ ይጠቁማል።
የኢንተርፕራይዙ ሰራተኞች ውሳኔያቸውን ለትምህርት ሚኒስቴር፣ ለጤና ሚኒስትር እና ለዩኒቨርስቲው የቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር መቅደስ ዳባ እንዲሁም ለሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ማሳወቃቸው ታውቋል።
በተመሳሳይ ከሰሞኑ የጤና ባለሙያችም "ጥያቄያችን ይመለስ" በሚል የመብት እና የጥቅም ጥያቄ በማንሳት በበርካታ የሀገሪቱ ክፍሎች ድምፅ እያሰሙ መሆናቸው ይታወቃል።
እነዚህ የጤና ባለሙያዎችም ለመንግስት ምላሽ መስጫ ቀን ሰጥተው እየጠበቁ ሲሆም ምላሽ ካላገኙ እስከ ስራ ማቆም የሚደርስ እርምጃ እንደሚወስዱ እያሳወቁ ይገኛሉ።
መረጃን ከመሠረት!




በደመወዝ አለመጨመር ምክንያት 2015ዓ.ም ስራ ለቅቄ አሁን የራሴን ስራ በመስራት ነኝ ለሰራተኞቹ መፍትሄ ሊሰጣቸዉ ይገባል
ለሙያው ብቻ ታማኝ በመሆን ከወገተኝነት የፀዳ ና እውነተኛ መረጃህ ተወዳጅ አድርጎኃል።