በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የሚሳተፉበት የተቃውሞ የበይነ መረብ ትዕይንተ-ህዝብ ሊዘጋጅ መሆኑ ታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- 'ጦርነት ይቁም! ሰላም ይምጣ!' በሚል ርዕስ የመቶ ሺዎች የተቃውሞ ትዕይንተ-ህዝብ በበይነ-መረብ አደባባይ ሊካሄድ መሆኑ ታወቀ።
"በንጹሀን ላይ እየደረሰ ያለውን ጭፍጨፋ የሚቃወምና በዓይነቱ የተለየ ታላቅ የተቃውሞ ትዕይንተ-ህዝብ ለማካሄድ እየተዘጋጀን ነው" በማለት የአብሮነት-ኢትዮጵያ ለሚድያችን የላከው መግለጫ ይጠቁማል።
ትዕይንተ-ህዝቡ የሚካሄደው ቅዳሜ ግንቦት 30 (ጁን 7) ቀን 2017 ዓ.ም ከቀኑ 11 ሰዓት (በዋሽንግተን 10AM፣ በለንደን 3PM) ጀምሮ እንደሚሆን የተገለፀ ሲሆን የአጀንዳው የጋራ ባለቤትና ተባባሪ የመሆን ፍላጐት ባላቸው በርካታ መገናኛ ብዙሀን በመላው ዓለም ለሚገኘው ኢትዮጵያዊ በቀጥታ ስርጭት ይተላለፋል ተብሏል።
"በዚህ ኢትዮጵያውያን የብሄር፣ የኃይማኖትና የርዕዮተ-ዓለም ልዩነት ሳያግዳቸው በጋራ በሚታደሙበት የበይነ-መረብ የተቃውሞ ትዕይንተ-ህዝብ ላይ በወቅቱ የተቃውሞ ትግል የመሪነት ወይም የጐላ የተሳትፎ ሚና ያላቸውና የተለያዩ የፖለቲካ አመለካከቶችንና ማህበረሰቦችን የሚወክሉ 15 ተዋቂ ሰዎች ተገኝተው ለህዝቡ የቀጥታ ንግግር ያደርጋሉ" የሚለው መግለጫው ንግግር እንዲያደርጉ የሚጋበዙት ታዋቂ ሰዎችም የሀገሪቱን የወደፊት ዕጣ-ፈንታ በመወሰን እረገድ የጐላ ሚና የሚኖራቸውና በአሁኑ ወቅት በሰላማዊ ወይም በትጥቅ ትግል ተሳትፎ ያላቸው ሰዎች ይሆናሉ ይላል።
አክሎም "ንግግር የሚያደርጉበት ርዕሰ ጉዳይም 'በሀገራችን ጦርነት ሊቆም፣ አገዛዝነት ሊያበቃና ዘላቂ ሰላም ሊመጣ እንዴት ይችላል?' በሚለው ወቅታዊ ጥያቄ ዙሪያ ይሆናል። በዚህ ትዕይንተ-ህዝብ ተቃውሞ የሚቀርብበት አገዛዝም ፈቃደኛነቱና ድፍረቱ ካለው በትዕይንተ-ህዝቡ ላይ ተገኝቶ አቋሙን እንዲገልፅ ይጋበዛል" በማለት መግለጫው አላማውን ያብራራል።
የትዕይንተ-ህዝቡ መሰረታዊ ዓላማ ተብለው የተዘረዘሩት:
"የኢትዮጵያ ህዝብ የመንግስትን የጦረኝነት አካሄድ ምን ያህል አምርሮ እንደሚቃወምና ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ እንደሚፈልግ በተግባር ለማሳየት፣
መንግስት የህዝቡን ሰላማዊ የተቃውሞ እንቅስቃሴ በተለመደ የአፈና ድርጊት አዳፍኖ ሊያስቀረው እንደማይችል በተግባር ለማሳየት፣
ተቃዋሚ ኃይሎች በልዩነቶቻቸው ላይ ከማተኰር ይልቅ ብሄር-ተሻጋሪ የሆነ ትብብር ፈጥረው ህዝቡን በጋራና በብቃት አታግለው ለአሸናፊነት መብቃት የሚችሉበት ዕድል መኖሩን ለማሳየት፣
በሀገራችን የሚዲያ የቀጥታ ስርጭት ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ትዕይንተ-ህዝቡን በ100ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮዽያውያን በአንድ ጊዜና በቀጥታ እንዲታደሙ በማድረግ አዲስና ተከታታይነት ያለው “አገዛዝ-አንቀጥቅጥ” የሆነ የሰላማዊ ትግል ተነሳሽነት በህዝቡ ውስጥ ለመፍጠር ነው" ብሏል።
የዚህን በዓይነቱ አዲስና ልዩ የሆነ ነው በተባለለት 'የትግል ስልት' ጠቀሜታ በመገንዘብ በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም የሚገኘው ኢትዮዽያዊ የትዕይንተ-ህዝቡን የቀጥታ ስርጭት በያለበት ቦታ ሆኖ በመሳተፍ ተቃውሞ እንዲገልፅ መጋበዙ ታውቋል።
ህዝብ በትዕይንተ-ህዝቡ እንዲሳተፍ የሚፈለገው በዩትዩብ /YouTube/ ወይም የረምብል /Rumble/ የቀጥታ ስርጭት ላይ መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን መገናኛ-ብዙሀን ትዕይንተ-ህዝቡን በዩትዩብ ወይም በራምብል በቀጥታ በማሰራጨትና አድማጮቻቸው የቀጥታ ስርጭቱን እንዲከታተሉ አስቀድመድ በስፋት በመቀስቀስ ዝግጅቱ ላይ እንዲሳተፉ ተጋብዘዋል።
መረጃን ከመሠረት!





በጣም አሪፍ ሃሳብ ነው።ስጋት ግን አለኝ፡እሱም ምንድን ነው መንግስት እንደዚህ አይነት ነገሮችን
ሲካሄዱ ተቀምጦ አያይም።ስለዚህ አላማውን ያሳካ እንቅስቃሴ እንዲሆን ጥንቃቄ ያስገልገዋል።ካልሆነ ግን እዛው በተቃውሞ ተጀምሮ የድጋፍ ትእይንት ሆኖ የመጠናቀቅ እድል አለው።
ምርጥ ሃሳብ ነው 🖋️