የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ መሠረት ሚድያ በኢሳያስ በላይ አሟሟት ዙርያ በሰራው የምርመራ ዘገባ ላይ ምላሽ ሰጠ
(መሠረት ሚድያ)- ሚድያችን ባሳለፍነው ቅዳሜ ግንቦት 9/2017 ዓ/ም በሰራው አንድ ዘገባው የዛሬ አመት በምርመራ ወቅት በደረሰበት ድብደባ ህይወቱ ስላለፈው የቀድሞው የኢንሳ እና የአማራ ባንክ ሰራተኛ ኢሳያስ በላይ አንድ የምርመራ ዘገባ ማውጣቱ ይታወሳል።
ልክ የዛሬ አመት በዚህ ወር ህይወቱ ያለፈው ኢሳያስ የአማራ ክልልን የሬዲዮ መገናኛ አውታር አቀናጅቶ ከተመለሰ ከሁለት ወር በኋላ የስራ መታወቂያውን ተቀምቶ ኢንሳ እንደተባረረ፣ ከዛም በአማራ ባንክ ተቀጥሮ እየሰራ እያለ ሚያዝያ 23 ቀን 2016 ዓ/ም ከምሽቱ 2:30 የፌደራል ፖሊሶች ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ትፈለጋለህ በሚል ይዘውት እንደወጡ፣ ከዛም ከሁለት ቀን በኋላ ከ14 ተጠርጣሪዎች ጋር ወደ አፋር ክልል ሰመራ ተወስዶ በምርመራ ወቅት በደረሰበት ድብደባ እጅግ የከፋ ጉዳት ደርሶበት ህይወቱ እንዳለፈ የምርመራ ሪፖርታችን ያሳያል (ሙሉ ሪፖርቱን ያንብቡ: https://tinyurl.com/yfbw5hm2
ይህን የምርመራ ዘገባ ተከትሎ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በዛሬው እለት በሶሻል ሚድያ ገፁ ባወጣው መግለጫ በኢሳያስ አሟሟት ዙርያ የተሰራጨው መረጃ 'ሀሰተኛ' ነው ብሏል።
ኢሳያስ በላይ የተባለው ግለሰብ በምርመራ ክፍል ውስጥ አሰቃቂ በሆነ ሁኔታ ተገደለ ተብሎ 'በአንዳንድ ሚዲያዎች' እየተዘዋወረ የሚገኘው መረጃ 'ሀሰተኛ' ነው ያለው መግለጫው በወቅቱ የተገኘው የሕክምና ማስረጃ የሚያሳየው የግለሰቡ ሕይወት ያለፈው በግል ጤና ችግር ምክንያት ነው ይላል።
አክሎም ለዚህም የወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ የሞቱን ምክንያት ለማረጋገጥ በወቅቱ የአስክሬን ምርምራ እንዲደረግ ዳግማዊ ሚኒሊክ ሪፈራል ሆስፒታልን ጠይቆ ሆስፒታሉም በላከው የአስክሬን ምርመራ ውጤት "በአካሉ ላይ የደረሰ ምንም ውጫዊ ጉዳት የሌለው መሆኑንና የግለሰቡ ሞት በሳምባ ምች በሽታ ምክንያት የደም ዝውውሩና የትንፋሽ ስርዓቱ በማቆሙ እንደሆነ ለኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አረጋግጧል" ይላል።
"የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ከሪፎርሙ በፊት እንደነበረው ኃይል የተቀላቀለበት ምርመራ የሚያካሄድ ሳይሆን አሁን ላይ ዓለም በደረሰበት ቴክኖሎጂ እየታገዘ ዛሬም ወደ ፊትም ሰብዓዊ መብትን የሚያከብርና ባህሉ አድርጎ የሚቀጥል መሆኑን በዚህ አጋጣሚ ያረጋግጣል" በማለት መግለጫው ያብራራል።
መሠረት ሚድያ ቅዳሜ እለት ለህዝብ ያስነበበው የምርመራ ዘገባው ትክክለኛ መሆኑን፣ ከበርካታ ምንጮች ያጣራው መሆኑን እንዲሁም እውነትነቱን የሚያስረዱ ተጨማሪ መረጃዎች ቢኖሩትም ለግዜው ለምንጮች ደህንነት ሲባል እንዳላወጣ ለአንባቢዎቹ ሊገልፅ ይወዳል።
ከዚህም በተጨማሪ ተጠርጣሪው እና ሌሎች ግለሰቦች ሲሰነዘርባቸው የነበረ ሚድያ ላይ ለመግለፅ የሚከብዱ በርካታ ፀያፍ ቃላቶች እንደነበሩ ልንገልፅ እንወዳለን።
መረጃን ከመሠረት!





አልሞተም ብለው ካልካዱንም ጥሩ ነው።
መሠረት ሚድያ ሁሌም የተረጋገጠ እና በማስረጃ የተደገፈ መረጃ ሲያቀርብ ኖሮዓል ይህ ዳግሞ ሚያስመሰግንና ሚበረታታ ነው ::