በአዳማ የታፈሱ ወጣቶች በፍየል ማቆያ መጋዘኖች ውስጥ ተይዘው ለመልቀቅ ገንዘብ እየተጠየቀባቸው መሆኑ ተሰማ
(ዜናመሠረት)- በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች በወጣቶች ላይ ያተኮረ መጠነ-ሰፊ የግዳጅ አፈሳ እና እገታ እየተካሄደ መሆኑ ከሰሞኑ በሚድያችን መዘገቡ ይታወሳል።
በአዳማ፣ በባህር ዳር፣ በቢሾፍቱ እና በሸገር ከተሞች ባሉ የተለያዩ አካባቢዎች በሚሊሻዎችና በጸጥታ ኃይሎች በወጣቶች ሰፊ የግዳጅ አፈሳ እየተካሄደ እንደሚገኝ የአይን እማኞችና ተጎጂዎች እየተናገሩ ይገኛሉ።
በአዳማ ከተማ ወንጂ ማዞሪያ በተባለ ቦታ በአካባቢው የሚገኙ ዘመዶቹን ጠይቆ ሲመለስ ታፍሶ ለሁለት ቀናት ያህል ታስሮ እንደነበር የገለጸ አንድ ወጣት "አፍሰው የወሰዱኝን ሰዎች በሰውና በስንት ልመና 20,000 ብር ከፍዬ ነው ልወጣ የቻልኩት" ሲሉ ለመሠረት ሚድያ ተናግሯል።
አክሎም ታፋሾቹ በአዳማ ከተማ ሞዮንኮ ጋራጅ ጀርባ በሚገኘውና በተለምዶ ሚዛን ተብሎ በሚጠራው ትልቅ የፍየል ማቆያ መጋዘን ውስጥ እንደሚታጉሩ ጠቁቆ "መክፈል የማይችሉ ወይም የሚያውቋቸው ሰው የሌላቸው ወደ መቶ የሚጠጉ ወጣቶች አሁንም በዚያ መጋዘን ውስጥ ይገኛሉ" ብሏል።
በተመሳሳይ ሁኔታ በባህር ዳር ከተማ ነሐሴ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በወጣቶች ላይ የተጠናከረ የግዳጅ አፈሳ መካሄዱን ከስፍራው የተገኙ መረጃዎች ያመለክታሉ።
በተለይም በቀበሌ 13፣ ጎፋ ሰፈር እና ገጠር መንገድ በተባሉ አካባቢዎች ስፋት ያለው አፈሳ የተካሄደ ሲሆን በርካታ እናቶች ልጆቻቸውን ፍለጋ በየፖሊስ ጣቢያው ሲንከራተቱ እንደነበርና በርካታ ወጣቶች በሲኖ ትራክ መኪናዎች ተጭነው ሲወሰዱ መታየታቸውን ነዋሪዎች መስክረዋል።
በቢሾፍቱ ከተማ አቅራቢያ በምትገኘው ድሎሎ ጂላ አካባቢ ደግሞ ሚሊሻዎች ወጣቶችን ከታክሲና ከባጃጅ በማስወረድ እያፈሱ መሆናቸው ታውቋል። አንድ የአይን እዩት እንደገለጹት ከሆነ "ረቡዕ ዕለት በዚሁ አካባቢ በሚገኘው ጊዳ ለታ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ቅጽረ ግቢ ውስጥ በቅዳሴ ላይ የነበሩ ወጣቶች ሳይቀሩ በጸጥታ አካላት ታፍሰው ተወስደዋል" ሲሉ የሁኔታውን አሳሳቢነት አስረድተዋል።
በሌላ በኩል በሸገር ከተማ በፉሪ፣ ኬንቴሪ፣ ሰበታ፣ አለምገና እና ወለቴ አካባቢዎች በሚሊሻዎች የሚካሄደው አፈሳ እጅግ ከባድ ደረጃ ላይ መድረሱ ተገልጻል።
በሚሊሻዎች የደፈጣ ድርጊት ምክንያት ወጣቶች ከቤት ወጥተው ዕቃ መግዛት እንኳን እንዳልቻሉ የተናገሩ አንድ የወለቴ ነዋሪ "በእኛ አካባቢ ብቻ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወጣቶች ታፍሰው ሀረር ዳቦ አካባቢ በሚገኘው የወጣቶች ማዕከል ውስጥ ታጉረዋል" ብለዋል።
ወላጆች ልጆቻቸውን ለመጠየቅ በሚሄዱበት ወቅት በሚሊሻዎች በዱላ እንደሚደበደቡና ከዚህ ቀደም ይደረግ የነበረው በገንዘብ ክፍያ የማስፈታት አሰራር አሁንም ቀጥሎ እንዳለ ገልጸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ትግራይን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚፈጸሙ መሰል ህገ-ወጥ እስራቶች እና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የዜጎችን የመንቀሳቀስ መብት በእጅጉ የገደቡት ሲሆን ወጣቶች ስራቸውን ትተው በቤታቸው ለመሸሸግ እንደተገደዱና የሚከላከልላቸው አካል በማጣታቸው ስጋት ላይ መውደቃቸውን አስታውቀዋል።
| መሠረት ሚድያ |



አሃሃሃ ብልፅግናችን እራሱ
በግዳጂ ወጣቱን እያፈሰ ነው ለካ
ሕወሓት ወጣቱን በግዳጂ እያፈሰ ነው
ብሎ የሚያታልለን