ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት እና የሕግ የበላይነት
በፍቅር ለይኩን የተፃፈ
(መሠረት ሚድያ)- በማንኛውም ዴሞክራሲያዊ ማኅበረሰብ ውስጥ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት እና የፕሬስ ነጻነት የሉዓላዊነትና የነጻነት መገለጫዎች ተደርገው ይወሰዳሉ። በተለይም በመገናኛ ብዙኃን የሚሠሩ ጋዜጠኞች የማኅበረሰቡን ድምፅ በማስተጋባት፣ የመንግሥትን አሠራር በመታዘብና ተጠያቂነትን በማስፈን ረገድ የጎላ ሚና አላቸው።
ይሁን እንጂ የፕሬስ ነጻነትና የብሔራዊ ደኅንነት ሚዛን፣ እንዲሁም በመንግሥት ጸጥታ ኃይሎች የሚወሰዱ እርምጃዎች ከሕገ-መንግሥታዊ ድንጋጌዎች ጋር ያላቸው መጣጣም በተደጋጋሚ ለክርክር የሚዳርግ ጉዳይ ነው።
ይህ ጽሑፍ በአገራችን ኢትዮጵያ ማንነትንና ሃይማኖትን ማእከል ባደረጉ ግድያዎችና ማፈናቀሎች ዙሪያ በሠራቻቸው ቪዲዮዎች ከሰሞኑን በቁጥጥር ስር የዋለችውንና ለ10 ቀናት ፍርድ ቤት ያልቀረበችውን የጋዜጠኛ ሣልሳዊት ባይነሳኝ ጉዳይ መነሻ በማድረግ- የኢትዮጵያን ሕገ-መንግሥት እና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ስምምነቶችን መሠረት በማድረግ ሙግታዊ ትንታኔ ያቀርባል።
1. ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ሕገ-መንግሥታዊና ዓለም አቀፋዊ መሠረቶች፤
የኢፌድሪ ሕገ-መንግሥት በአንቀጽ ፳፱ (29) ላይ ማንኛውም ሰው ያለ ምንም ጣልቃ ገብነት የፈለገውን ሐሳብ የመያዝ፣ የመግለጽና መረጃ የመሰብሰብ እንዲሁም የማሰራጨት መብት እንዳለው በግልጽ ይደነግጋል። ይህ መብት በተለይ የፕሬስ ነጻነትንና የሚዲያ ተቋማትን ሥራ የሚመለከት ሲሆን ሳንሱር በሕግ የተከለከለ መሆኑንም ያረጋግጣል።
ከዚህ በተጨማሪ ኢትዮጵያ ተቀብላ ያጸደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ለምሳሌ፤
የዓለም አቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን (ICCPR) አንቀጽ 19፤
የአፍሪካ የሰዎችና የሕዝቦች መብቶች ቻርተር (ACHPR) አንቀጽ 9፤
እነዚህ ሰነዶች ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት የሰብአዊ መብቶች ሁሉ መሠረት መሆኑን ያስገነዝባሉ። ከንድፈ-ሐሳብ አንጻር እንደ John Stuart Mill ያሉ ምሁራን፤ "የሐሳብ የገበያ ቦታ" (Marketplace of Ideas) በሚለው እሳቤያቸው፤ እውነት ሊገኝ የሚችለው ሐሳቦች በነጻነት ሲንሸራሸሩና ክርክር ሲደረግባቸው ብቻ እንደሆነ ይከራከራሉ።
በመሆኑም ጋዜጠኞች በማኅበረሰቡ ውስጥ ያሉ አስከፊ እውነታዎችን (እንደ ማፈናቀልና ግድያ ያሉ) ይፋ ማድረጋቸው የሙያዊ ኃላፊነትና የሕዝብን መረጃ የማግኘት መብት የማክበር ጉዳይ ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል።
2. የፍጹምነት ወሰን እና የብሔራዊ ደኅንነት ሚዛን፤
ምንም እንኳን ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት መሠረታዊ ቢሆንም ፍጹም (Absolute) አይደለም። የኢፌድሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 29(6) እንዲሁም የ-ICCPR አንቀጽ 19(3) መብቱ ገደብ ሊጣልበት የሚችልባቸውን ሁኔታዎች ያስቀምጣሉ።
እነዚህም የሌሎችን መብትና ክብር ለመጠበቅ፤
ብሔራዊ ደኅንነትን፣ የሕዝብን ሰላምና ጸጥታን እንዲሁም የሕዝብን ጤና ወይም ሥነ-ምግባር ለመጠበቅ ሲባል ነው።
የሙግት ነጥብ፡- በሀገሪቱ ስሱ የሆኑ የማንነትና የሃይማኖት ጉዳዮችን ይፋዊ የቪዲዮ ምስሎችንና ጽሑፎችን ማጋራት በአንድ በኩል ግልጽነትንና እውነትን ማውጣትን የሚያበረታታ ሲሆን፤ በሌላ በኩል ደግሞ ይዘቶቹ የጥላቻ ንግግርን (Hate Speech) የሚያነሳሱ፣ ወይም ግጭትን የሚቀሰቅሱ ከሆኑ በሕግ ሊጠየቁ የሚችሉበት ዕድል አለ።
ሆኖም ግን ይህ ገደብ ሥራ ላይ ሊውል የሚችለው በሕግ የተደነገገ (Prescribed by Law)አስፈላጊ (Necessary) እና ተመጣጣኝ (Proportional) በሆነ መንገድ ብቻ መሆን እንዳለበት የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችና ምሁራን ይከራከራሉ። ጋዜጠኛን ማሰር የመጨረሻ አማራጭ (Ultima Ratio) መሆን ያለበት እንጂ የዜጎችን የመረጃ ፍሰት መግቻ መሣሪያ መሆን የለበትም።
3. የ48 ሰዓት ሕገ-መንግሥታዊ ግዴታ እና የሕግ የበላይነት መሸርሸር፤
የዚህ ጉዳይ ዋነኛውና አሳሳቢው ሕጋዊ ጥሰት የሚጀምረው ጋዜጠኛዋ በቁጥጥር ስር ከዋለች በኋላ ከተፈጸመው የአያያዝ ሂደት ነው። የኢፌድሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ ፲፱ (፫) በግልጽ እንደሚያስቀምጠው፦
"የተያዙ ሰዎች በቁጥጥር ስር በዋሉ በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት አላቸው። ይህ ጊዜ ተያዙበት ቦታ ወደ ፍርድ ቤት ለመምጣት ከሚያስፈልገው ተገቢ ጊዜን አይጨምርም ነፃነታቸውን እንዳያጡ ለመከላከል ወዲያውኑ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት አላቸው።"
ይህ ድንጋጌ የፓርላማ ሕግ ሳይሆን፣ የሀገሪቱ የበላይ ሕግ (Supreme Law) ነው። ጋዜጠኛዋ ላለፉት 10 ቀናት ፍርድ ቤት ሳትቀርብ መቅረቷ ይህንን ሕገ-መንግሥታዊ መሠረት በግልጽ የጣሰ ድርጊት ነው።
ምሁራዊና ተጠየቃዊ ትንታኔ (Theoretic and Philosophical Perspective)፤
ሐቤስ ኮርፐስ (Habeas Corpus)፦ ይህ መርህ በሕግ ታሪክ ውስጥ ግብረ-ገብነትንና ፍትሕን ለማስፈን ከተቀረጹ ትልልቅ መርሆዎች አንዱ ነው። ትርጉሙም "አካሉን ይዘህ ቅረብ" ማለት ሲሆን አስፈጻሚው አካል (የጸጥታ ኃይሉ) አንድን ዜጋ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ለረጅም ጊዜ አፍኖ እንዳያቆይ የሚከላከል የነጻነት ጋሻ ነው።
የሥልጣን ክፍፍል መርህ (Separation of Powers)፦ በቻርለስ ደ ሞንቴስኪው (Montesquieu) ፍልስፍና መሠረት፣ የሕግ አስፈጻሚው አካል (ፖሊስ/ጸጥታ) ሰዎችን የመያዝ ሥልጣን ቢኖረውም የእስሩን ሕጋዊነት የመመርመርና የመወሰን ሥልጣን ሙሉ በሙሉ የሕግ ተርጓሚው (የፍርድ ቤት) ብቻ ነው።
ፖሊስ አንድን ዜጋ ለ10 ቀናት ፍርድ ቤት ሳይልክ ሲያቆይ ራሱን በሕግ ተርጓሚነት ቦታ ላይ እየሰየመ መሆኑን ያሳያል። ይህ ደግሞ ወደ አምባገንነትና ወደ ሕግ አልባነት (Arbitrary Detention) የሚወስድ አደገኛ መንገድ ነው።
የጸጥታ ኃይሎች የሚዲያ ይዘቱ "የሀገር ደኅንነትን ይነካል" የሚል እምነት ቢኖራቸው እንኳ ያንን እምነታቸውንና ያሏቸውን ማስረጃዎች በ48 ሰዓት ውስጥ ለገለልተኛ ዳኛ አቅርበው የተጨማሪ ምርመራ ጊዜ (Remand) መጠየቅ ነበረባቸው። ይህ ሳይሆን መቅረቱ የእስሩን ሕጋዊነት ሙሉ በሙሉ ጥያቄ ውስጥ የሚጥለውና የመንግሥትን ሕግ የማክበር ግዴታ (Duty to Respect) የሚሸረሽር ነው።
መደምደሚያ፤
ጋዜጠኝነት ወንጀል አይደለም ይልቁንም የማኅበረሰብን ሕመም የሚያሳይ መስተዋት ነው። በማንነትና በሃይማኖት ላይ የሚፈጸሙ ግድያዎችንና መፈናቀሎችን ወደ አደባባይ ማውጣት፣ መንግሥት ኃላፊነቱን እንዲወጣ የሚያስገድድ የሕዝብ ድምፅ ሊሆን ይችላል።
የይዘቱ አግባብነትና ሕጋዊነት ጥያቄ ውስጥ የሚወድቅ ቢሆን እንኳ ሊፈታ የሚገባው በሕገ-መንግሥታዊና በሕጋዊ ሥርዓቶች መዋቅር ውስጥ ብቻ ነው።
አንድን ጋዜጠኛ ለ10 ቀናት ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ማሰር ሕገ-መንግሥቱን መጣስ ብቻ ሳይሆን፣ በሀገሪቱ የዲሞክራሲ ምኅዳር ላይ የፍርሃት ጥላ (Chilling Effect) የሚያሳድር ድርጊት ነው።
መንግሥት የሕግ የበላይነትን ለማስከበር መጀመሪያ ራሱ በሕግ መገዛት አለበት። ስለሆነም ጋዜጠኛዋ በአስቸኳይ ፍርድ ቤት ልትቀርብ ወይም ሕገ-መንግሥታዊ መብቷ ተከብሮ በአፋጣኝ ልትፈታ ይገባል።
ሕግን ለመጠበቅ በሚደረግ ጉዞ ውስጥ ሕግን መጣስ፣ ራሱ ሌላ የሕግ መፍረስን የሚወልድ በመሆኑ ሥርዓቱ ሊታረም ይገባዋል።
***መሠረት ሚድያ ላይ የሚቀርቡ አስተያየቶች በሙሉ የፀሀፊዎቹ እንጂ የሚድያው አቋም እንዳልሆኑ ልናስታውስ እንወዳለን።
| መሠረት ሚድያ |


