በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ውስጥ ያለውን የአንዳንድ ሰራተኞች የፎርጅድ ዶክመንት ያጋለጠው ሰራተኛ ታሰረ
(መሠረት ሚድያ)- የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) አንዳንድ ሰራተኞች ፎርጅድ ወይም እውቅና የሌለው የትምህርት ማስረጃ እንዳላቸው ያጋለጠው የተቋሙ ሰራተኛ ባሳለፍነው እሮብ እለት መታሰሩ ታውቋል።
መሠረት ሚድያ የደረሰው መረጃ እንደሚጠቁመው አቶ ወገን አበበ የተባለው ግለሰቡ ከመኖርያው ዲላ ከተማ በፀጥታ ሀይሎች ተይዞ ወደ ወላይታ ከተማ ተወስዷል።
የዲላ ከተማ የፀጥታ አካላት አቶ ወገንን 'ከላይ ታዘን ነው' በሚል ምክንያት እንደያዙት እና አሁን ላይ ማንም የሚረዳው በሌለበት እና በማያውቀው ከተማ እንዲታሰር መደረጉን ምንጮቻችን ጠቁመዋል።
እሮብ እለት ከተያዘ በኋላም 'ሀሰተኛ መረጃ አሰራጭተሀል' ሲሉት እንደነበርና እስካሁን ፍርድ ቤት እንዳልቀረበ ታውቋል።
የቀድሞ የተቋሙ ሰራተኞ የሆኑት አቶ ወገን ከዚህ በፊትም ጥር ወር ላይ ታስረው የሽብር ክስ ቀርቦባቸው እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል።
በወቅቱ 52 ቀን ታስረው ጥር 26/2017 ዓ. ም ተለቀው ነበር። "የተያዝኩት ተወልጄ ባደግኩባት ዲላ ከተማ ነው፣ ከላይ በመጣ ትእዛዝ ተብሎ ቤቴ ተበረበረ። ዲላ 5 ቀን ከታሰርኩ በኋላ ወደ ወላይታ ሶደ ተወሰድኩ፣ 3 ቀን ታስሬ ወደ ሀዋሳ የፌደራል ምርመራ ተወሰድኩ፣ ከዛም አንድ ሳምንት ሀዋሳ ታስሬ ወደ አዲስ አበባ ፌደራል ምርመራ ሜክሲኮ ተወሰድኩ" በማለት ያለፈበትን የእስር ሂደት በወቅቱ ለሚድያችን አስረድቶ ነበር።
መሠረት ሚድያ ጥር ወር ላይ የተመለከተው የክስ ወረቀት እንደሚለው አቶ ወገን በአማራ ክልል ከሚንቀሳቀሱ ፀረ ሰላም ቡድን አባሎች ጋር በመቀናጀት እና ቡድኑን በመምራት መጠርመሩን ይገልፃል።
ክሱ አክሎም "በሀገራችን የተለያዩ አካባቢዎች ጥቃት ለማድረስ ተልእኮ በመቀበል እና ቡድኑን በገንዘብ በማገዝ" እንዲሁም "በመላው ሀገራችን ሰላም እንደሌለ በማስመሰል ህዝብ በመንግስት ላይ እንዲነሳሳና ለሽብር ተግባራት የሚቀሰቅሱ የሀሰት ቪድዮ እና የድምፅ መልዕክት በማዘጋጀት እና በማህበራዊ ሚድያ በማሰራጨት" የሚሉ ውንጀላዎችን አካቷል።
ይሁንና በወቅቱ አቶ ወገን ከ52 ቀን እስር በኋላ በ40 ሺህ ብር ዋስ ተለቀዋል።
"እኔ አማራ ክልል ሄጄ እንኳን አላውቅም፣ ዘመድም የለኝም" የሚለው አቶ ወገን እንኳን ለተለያዩ ቡድኖች የገንዘብ ድጋፍ ሊያደርግ ኢቢሲ ከስራው ካባረረው በኋላ ስራ እንኩዋን እንደሌለው ገልጿል።
ግለሰቡ ከአንድ አመት በፊት የአንዳንድ የኢቢሲ ሰራተኞች የፎርጂድ ዶክመንትን በተመለከተ ካጋለጠ በኋላ ተቋሙ መረጃውን ያወጣብኝ የቀድሞ ሰራተኞዬ "ተአማኒነቴ እንዲቀንስ አድርጓል" በማለት 10 ሚልዮን ብር ካሳ ይክፈለኝ ብሎ ክስ መስርቶም ነበር።
ይሁንና ራሱ ኢቢሲ ከወራት በፊት በተቋሙ ሰራተኞች ላይ ባደረገው የትምህርት ማስረጃ ማረጋገጥ ሂደት የ400 ሰራተኞቹ ሰነድ ፎርጂድ/ሀሰተኛ መሆኑን እንዳረጋገጠ አንድ ሾልኮ የወጣ ዶክመንት ጠቁሞ ነበር።
ይህ ሆኖ እያለ የተቋሙ ሀላፊዎች እርምጃ እንዳይወሰድ ይህን መረጃው እንደደበቁ፣ በጥቆማ አቅራቢዎች ላይም ዛቻ እና ማስፈራርያ እያደረሱ እንደኮነ በወቅቱ የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ለጠቅላይ አቃቤ ህግ የፃፈው ደብዳቤ አሳውቆ ነበር።
መረጃን ከመሠረት!




