ማቆሚያ በሌለው የግዳጅ መዋጮ የተማረሩ አንዳንድ የኮዬ ፈጬ እና የቱሉ ዲምቱ ኮንዶሚኒየም ነዋሪዎች አካባቢውን ለቀው መሰደድ መጀመራቸው ተሰማ
(መሠረት ሚድያ)- ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ የነበሩ፣ ከሦስት ዓመት ተኩል በፊት በነበረው የአስተዳደር ወሰን ለውጥ ወደ ሸገር ከተማ የተካለሉ የኮዬ ፈጬ እና የቱሉ ዲምቱ የኮንዶሚኒየም ነዋሪዎች ለመሠረት ሚድያ ተከታታይ መልዕክቶችን ሲያደርሱ ቆይተዋል።
ነዋሪዎቹ በአሁኑ ወቅት በአካባቢያቸው እየተተገበረ ያለው የመዋጮ አሠራር የኅብረተሰቡን የመክፈል አቅምና ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ፣ አንዱ ሲያልቅ ሌላው የሚተካ ማባሪያ የሌለው የግፍ መዋጮ በመሆኑ ለከፍተኛ ምሬት ተዳርገናል ይላሉ።
"የአካባቢያችን ማኅበረሰብ በአብዛኛው በከፍተኛ ድህነት ውስጥ የሚገኝ፣ የዕለት ጉርስ ለማግኘትና ልጆቹን ለማስተማር እጅግ እየተቸገረ ያለ ቢሆንም አስተዳደሩ ግን ይህንን ችላ በማለት በሚከተሉት አስገዳጅ ክፍያዎች ሕዝቡን እያስለቀሰ ይገኛል" የሚሉት አንድ የቤተሰብ አስተዳዳሪ አባት ናቸው።
ሚድያችን የደረሱት መረጃዎች እንደሚያሳዩት ተደራራቢ መዋጮዎቹ ለሚሊሻ፣ ለቡሳ ጎንፋ ማህበር እና ለኦሮሚያ ልማት ማኅበር የሚል ይገኝበታል።
ከጣራና ግድግዳ ግብር ጋር ተዳምሮ ከ3,500 ብር በላይ መክፈላቸውን፣ በተጨማሪም የጣራና የግርግዳ ግብር በካሬ 133 ብር፣ ለኮብልስቶን መንገድ 2,000 ብር፣ ለቤት ቀለም መቀቢያ 10,000 ብር፣ ለዞን ጽሕፈት ቤት ማስገንቢያ 500 ብር፣ ለግቢ ውስጥ ቴራዞ ሥራ 5,000 ብር እንደከፈሉ ለሚድያችን ማስረጃ አቅርበዋል።
ከሰሞኑ ደግሞ "ከሸገር ከተማ የወረደ መመሪያ ነው" በሚል በአንድ የቤት ማኅበር ፓርሴል (ብሎክ) ውስጥ 17 ካሜራዎች እንዲገጠሙ እየተነገራቸው ይገኛል።
"እኛ ነዋሪዎቹ በጋራ አጥር አጥረን፣ የራሳችንን የጥበቃ ሠራተኛ ቀጥረን በሰላም እየኖርን ባለንበትና ሌባ አስቸገረን ብለን ቅሬታ ባላቀረብንበት ሁኔታ ይህ የካሜራ ክፍያ መጫኑ አግባብነት የሌለው ብዝበዛ ነው" የሚሉት ሌላ ነዋሪ ናቸው።
አክለውም "ከነዚህ ሁሉ መዋጮዎች በተጨማሪ የትራንስፖርት ዋጋ ጭማሪው ወገቡን አጎብጦታል። መሀል ከተማ ሄዶ ሠርቶ የሚገባውን ሰው ትተን ወደ መገናኛ ብቻ ለመድረስና ለመመለስ በታክሲ በቀን 120 ብር፣ በአውቶቡስ ደግሞ 60 ብር ይጠይቃል። ይህ ወጪ በወር ሲታሰብ ብቻውን ምን ያህል የኑሮ ጫና እንደሚፈጥር መገመት ይቻላል። ሕዝቡ በልቶ ለማደር በሚታገልበት በዚህ አስቸጋሪ ወቅት እነዚህ መዋጮዎች የሕዝቡን አቅምና ፍላጎት በፍጹም ያላገናዘቡ ናቸው" በማለት ያስረዳሉ።
ክፍያውን መፈጸም የማይችሉ ዜጎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ምሕረት የሌለውና አስገዳጅ መሆኑን ደጋግመው የሚኔገሩት ነዋሪዎቹ ብዙዎች ይህንን መባቻ የሌለው መዋጮ መቋቋም አቅቷቸው ቤታቸውን ሸጠው ለመውጣትና ወደ ሌላ አካባቢ ተሰደው ተከራይቶ ለመኖር እየተገደዱ ይገኛሉ።
-መሠረት ሚድያ-



