የቤት ኪራይ ጭማሪ ጣሪያውና ያስከተለው ውዝግብ: አዲሱ መመሪያ በአከራዮችና በሕዝብ ዘንድ የፈጠረው ስጋትና ቅሬታ
(መሠረት ሚድያ)- የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት ቢሮ ለዘንድሮው በጀት ዓመት የቤት ኪራይ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ብቻ እንዲሆን መወሰኑንና ይህንን ሕግ በሚተላለፉ አከራዮች ላይ እስከ ሦስት ወር የኪራይ ክፍያ የሚደርስ ከባድ የገንዘብ ቅጣት እንደሚጣል ማስታወቁ ይታወሳል።
ቢሮው ውሳኔው የተከራዮችን የመክፈል አቅም እና የኑሮ ውድነትን ያገናዘበ ጥልቅ ሳይንሳዊ ጥናት ተካሂዶበት የተወሰነ ነው ቢልም መመሪያው ይፋ መደረጉን ተከትሎ ግን ከሕዝብና ከአከራዮች ዘንድ ጠንከር ያሉ ቅሬታዎችና ስጋቶች እየተሰነዘሩበት ይገኛል።
የከተማ አስተዳደሩ አዲሱን መመሪያ ተፈጻሚ ለማድረግ በርካታ አሠራሮችን ፈጽሞ የከለከለ ሲሆን ጥሰት በሚፈጽሙ አካላት ላይ ጠንካራ አስተዳደራዊና ሕጋዊ እርምጃዎችን እንደሚወስድ በይፋ አስጠንቅቋል።
በዚህ አዲስ አሠራር መሰረት ከተቀመጠው የ11.5% ዓመታዊ የቤት ኪራይ ጭማሪ ጣሪያ በላይ መጨመር ወይም በተለያዩ ምክንያቶች ዋጋ ማናር በጥብቅ የተከለከለ ነው።
ከዚህ በተጨማሪ በየደረጃው በሚገኝ የቤቶች ልማትና አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ሳይመዘገብና ዕውቅና ሳይሰጠው በአከራይና ተከራይ መካከል ብቻ የሚደረግ ማንኛውም ዓይነት የመንደር ውል ወይም የውስጥ ስምምነት በሕግ ፊት ዋጋ እንዳሌለውና የተከለከለ መሆኑ ተገልጿል።
የመኖሪያ ቤት ኪራይ ውል ዕድሳት ምዝገባን አለመፈጸም ወይም መሸሽ፣ ቀደም ሲል ሲከራይ የቆየን ወይም ግንባታው የተጠናቀቀ አዲስ መኖሪያ ቤት ያለአገልግሎት ማቆየት፣ እንዲሁም የመኖሪያ ቤት ኪራይ ክፍያን በባንክ ወይም በሕጋዊ የኤሌክትሮኒክስ መንገድ አለመፈጸም አስተዳደራዊ ቅጣትን የሚያስከትሉ የተከለከሉ ተግባራት ናቸው።
መመሪያው የወጣው ተከራዮችን ከተጋላጭነት ለመጠበቅና መረጋጋትን ለመፍጠር እንደሆነ ቢሮው ቢገልጽም ይፋ የተደረጉት ክልከላዎችና የቅጣት እርምጃዎች ግን በሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ የደኅንነት ስጋትና የተቃውሞ ድምፅ አስነስተዋል።
በርካታ አስተያየት ሰጪዎች መመሪያው በሕገ-መንግስቱ አንቀፅ 40 እና 41 ላይ የተደነገገውን ዜጎች ንብረት የማፍራት፣ በንብረታቸው የመጠቀምና በመረጡት የኢኮኖሚ ዘርፍ የመሳተፍ መብትን የሚጥስ ነው በማለት በጽኑ ይሞግታሉ።
መንግስት ራሱ ባልሰራውና ባላገዘበት የግለሰብ ቤት ላይ የዋጋ ተመን በመቁረጥ ፈላጭ ቆራጭ መሆኑ አግባብ እንዳልሆነና አከራዮችን መብት የሚነፍግ እንደሆነ አስተያየቶች እየተሰጡ ይገኛሉ።
የብዙዎች ትችት እንደሚያሳየው በከተማዋ ያለው ትልቁ ችግር የቤት ኪራይ መወደድ ብቻ ሳይሆን የተሳሳተ የኢኮኖሚ ፖሊሲ የወለደው የኑሮ ውድነትና የሕዝቡ የመክፈል አቅም መዳከም ነው።
በገበያ ላይ ያሉ ሌሎች የፍጆታ ዕቃዎችና አገልግሎቶች ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ባለበትና የብር የመግዛት አቅም በወረደበት ሁኔታ በአከራዮች ላይ ብቻ የዋጋ ገደብ መጣሉ ፍትሐዊ እንዳልሆነና የሕዝብን ጉዳት ይበልጥ እንደሚጨምረው ተገልጿል።
በተለይም ደግሞ በከተማዋ የሚኖሩ በርካታ ጡረተኞች፣ አቅመ-ደካሞች እና ስራ የሌላቸው ዜጎች ኑሯቸውን የሚደጉሙት በቤት ኪራይ ገቢ በመሆኑ ይህ መመሪያ እነዚህን ተጋላጭ ወገኖች ይበልጥ የሚያደኸይና የኑሮ ዋስትናቸውን የሚያጣጣ ብስለት የሌለው ውሳኔ ነው ሲሉ ተቺዎች ይገልጹታል።
ለአሁኑ የቤት እጦት ችግር ዋናው ተጠያቂ መንግስት ራሱ እንደሆነና ላለፉት ዓመታት በቂ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን አለማቅረቡ ችግሩን እንዳባባሰው ይነገራል።
ከዚህም በላይ ለኮሪደር ልማት በሚል በርካታ ሺህ ቤቶች መፍረሳቸው፣ እንዲሁም በየአካባቢው ባለው የፀጥታ ችግር ምክንያት በርካታ ሕዝብ ወደ አዲስ አበባ መፍለሱ ለቤት እጥረቱና ለዋጋው መናር መሰረታዊ ምክንያቶች መሆናቸውን አስተያየት ሰጪዎች ይጠቅሳሉ።
መሰረታዊውን የአቅርቦትና ፍላጎት አለመመጣጠን ሳይፈቱ ጉዳዩን በሕግና በማስፈራራት መንገድ ለመፍታት መሞከር ችግሩን ይበልጥ እንደሚያወሳስበውና በአከራይና ተከራይ መካከል ያለውን ሰላማዊ ግንኙነት ሊያሻክር እንደሚችል ስጋቶች አሉ።
በአጠቃላይ ውሳኔው በተግባር ሲውል አከራዮች ቤቶቻቸውን ከገበያ እንዲያስወጡ ወይም ይበልጥ ድብቅ የሆኑ ሕገ-ወጥ አሠራሮች እንዲበራከቱ በር ከፋች ሊሆን እንደሚችል የብዙዎች ስጋት ነው።
| መሠረት ሚድያ |


