ከአስር ሺህ ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ መገበያየት ቅጣት ሊጣልበት መሆኑ ተሰማ
(መሠረት ሚድያ)- በግብይት ወቅት ከ10 ሺህ ብር በላይ ጥሬ ገንዘብን መጠቀም ለከፋዩ በወጪነት፣ ለተቀባዩ ደግሞ አስተዳደራዊ ቅጣት እንዲጣልበት ያደርጋል ተባለ።
አዲሱ የገቢ ግብር አዋጅ ሲጸድቅ ከ10,000 ብር በላይ ግብይትን በጥሬ ገንዘብ መፈጸም የሚያስቀጣ ይሆናል ተብሏል።
ረቂቅ አዋጁ ላይ ሃሳብ ለማዋጣት ከተሳተፉ ባለሙያዎች የተወሰኑት ተግባራዊ ይደረጋል በተባለው አሰራር ላይ ጥያቄ አንስተዋል።
ሸገር እንደዘገበው የገንዘብ ሚኒስቴር የህግ ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊው አቶ ተወዳጅ መሐመድ አዋጁ ተግባራዊ የሚደረገው በጥሬ ገንዘብ የሚፈፀም ግብይትን መገደብን ታሳቢ አድርጎ ነው።
በአንድ ግብይት የሚፈፀም የጥሬ ገንዘብ ክፍያ ከ10 ሺህ ብር ከበለጠ ትርፉ ብር ለከፋዩ በወጪነት አይያዝም። ገንዘቡን የተቀበለውም የትርፉን ገንዘብ እጥፍ አስተዳደራዊ ቅጣት እንደሚጣልበት ተቀምጧል ተብሏል።
ለምሳሌ የ20 ሺህ ብር ግብይት በጥሬ ገንዘብ ቢፈፀም ለነጋዴው ከ10 ሺህ ብር በላይ ያለው በወጪነት አይያዝም፣ ለተቀባዩ ደግሞ ከ10 ሺህ በላይ ያለው ቀሪ 10 ሺህ ብር እጥፍ ማለትም 20 ሺህ ብር ይቀጣል እንደማለት ነው።
በረቂቅ አዋጁ ላይ የተሳተፉ በጥሬ ገንዘብ ግብይት እንዲፈፀም ምክንያት የሚሆነውን በንግድ ስርዓቱ ውስጥ ያለውን ችግር መፍታት የተሻለ አማራጭ ሊሆን እንደሚችልና በሌሎች መመሪያዎች የጥሬ ገንዘብ ግብይት ስለሚፈቀድ አዋጁ የተናበበ እንዲሆን ጠይቀዋል።
የገንዘብ ሚኒስቴር ባሰናዳው ረቂቅ አዋጅ መሰረት ከ10 ሺህ ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ ግብይት እንዳይፈፀም የሚጣለው ግዴታ በመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ በመንግስት የልማት ድርጅቶች፣ በባንኮችና በማይክሮ ፋይናንስ ድርጅቶች ላይ ተፈጻሚ አይሆንም ይላል።
ሌሎች አዋጁ ተፈፃሚ የማይሆንባቸው ግለሰቦችና ድርጅቶች የገንዘብ ሚኒስቴር በሚያወጣው መመሪያ ዝርዝራቸው ይፋ ይሆናል ይላል ረቂቁ።
Via Sheger



