የትናንት የፕሬዝደንት ትረምፕ ንግግርን ተከትሎ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአሜሪካውን አምባሳደር ጠርቶ አነጋገረ
(መሠረት ሚድያ)- የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትረምፕ በትናንትናው እለት ሀገራቸው በህዳሴ ግድብ ዙርያ ኢትዮጵያ እና ግብፅ በሚወዛገቡበት ጉዳይ 'ስራ እየሰራንበት ነው' በማለት ተናግረው ኢትዮጵያ የናይል ወንዝን እየዘጋች ነው የሚል ንግግር ሲያደርጉ ተደምጠው ነበር።
ፕሬዝደንቱ "እኔ ግብፅን ብሆን ናይል ወንዝ ውስጥ ውሀ እንዲኖር እፈልጋለሁ። እሱ ችግር ላይ ስራ እየሰራንበት ነው፣ ይፈታልም። በአለም ትልቅ ከሚባሉት ግድቦች አንዱን ከግብፅ ወጣ ባለ ቦታ ነው የገነቡት... ያ ደግሞ ትልቅ ችግር ሆኗል" ብለው ነበር።
ይህን ተከትሎ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ የአሜሪካውን አምባሳደር ኧርቪን ማሲንጋን በቢሯቸው ጠርተው ማነጋገራቸው ታውቋል።
"ውይይቱ በዋናነት በትናንትናው እለት እንዲሁም ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ፕሬዝደንት ዶናልድ ትረምፕ በህዳሴ ግድብ እና በናይል ወንዝ ዙርያ ባረጉት ንግግር ላይ ያተኮረ ነበር። የኢትዮጵያን እውነት እና መሬት ላይ ያሉ ሀቆችን እንዲረዱት ተደርጓል" በማለት አንድ ጉዳዩን የሚያውቁ ዲፕሎማት ለመሠረት ሚድያ ተናግረዋል።
ይህ ውይይት እንደተካሄደ የሚጠቁም አንድ አጭር መረጃ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፌስቡክ ገፅ ላይ ይህ ዜና ከመውጣቱ ከደቂቃዎች በፊት መለቀቁንም ተመልክተናል።
አሜሪካ የግድቡን ወጪ እንደቻለች በትናንት ንግግራቸው ላይ የጠቀሱት ፕሬዝደንቱ የናይል ወንዝ የግብፅ 'ህይወት' መሆኑን ሲናገሩ ተደምጠዋል። "ይህንን ደግሞ መውሰድ እጅግ አስገራሚ ነው፣ ይህንን በፍጥነት እንፈታዋለን" በማለት ተናግረዋል።
በሌላ በኩል የግብፁ ፕሬዝደንት አብደልፈታህ አል-ሲሲ ትናንት ፕሬዝደንት ትረምፕ ያረጉትን ንግግር አድንቀው ለውዝግቡ መፍትሄ እንዲሰጠው ከልባቸው የሚፈልጉ መሪ ናቸው በማለት በኦፊሴላዊ የማህበራዊ ሚድያ ገፆቻቸው ላይ በዛሬው እለት መረጃ አጋርተዋል።
በመሪ ደረጃ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ለዶናልድ ትረምፕ ንግግር እስካሁን ምላሽ አልተሰጠም።
ኢትዮጵያ ከአለም አቀፍ አበዳሪ ተቋማት ገንዘብ በማግኘት በአባይ ወንዝ ላይ የሀይድሮ ኤሌክትሪክ ግድብ ለመገንባት ለበርካታ አመታት ብዙ ሙከራ አድርጋ የነበረ ቢሆንም በግብፅ ተፅእኖ አለመሳካቱ ይታወቃል።
በዚህም ምክንያት የዛሬ 13 አመት የህዳሴ ግድብን በራስ ወጪ ለመገንባት እቅድ ተነድፎ እንቅስቃሴ መጀመሩን መንግስት ገልፆ ነበር።
የህዳሴ ግድብ በመጪው መስከረም ወር ላይ ግንባታው ተጠናቆ እንደሚመረቅ ይጠበቃል።
መረጃን ከመሠረት!
Photo: MoFA Ethiopia



