ዶ/ር ሀብታሙ አለሙ ድሬዳዋ በእስር ላይ እንዳሉ እየታወቀ የሚሠሩበት ድል ጮራ ሆስፒታል የሥራ ጥሪ አደረገ
(መሠረት ሚድያ)- በድሬዳዋ ከተማ በሕክምና ባለሙያነት የሚያገለግሉትና በቅርቡ በተካሄደው 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የግል የፓርላማ እጩ ተወዳዳሪ የነበሩት ዶ/ር ሀብታሙ አለሙ ሸዋ ያለዋስትና ለ30 ቀናት በቁጥጥር ስር መዋላቸውንና ተከታታይ አስተዳደራዊ ጫናዎች እየተፈጸሙባቸው መሆኑን ምንጮች ለሚድያችን ጠቁመዋል።
ሚድያችን የደረሰው መረጃ እንደሚጠቁመው ዶ/ር ሀብታሙ ያለ ፍርድ ቤት ማዘዣ በድሬዳዋ ፖሊስ ታፍነው ከተወሰዱ በኋላ በአሁኑ ወቅት በከዚራ ፖሊስ ጣቢያ በእስር ላይ ይገኛሉ።
"ፖሊስ የምርመራ ጊዜን በተለያየ መልኩ በማራዘሙ ምክንያት ፍርድ ቤቱ መጀመሪያ የሰጠውን የ14 ቀናት ቀጠሮ ጨምሮ ለሁለተኛ እና ለሦስተኛ ጊዜ ተጨማሪ የስምንት ቀናት ቀጠሮዎችን በተከታታይ በመፍቀድ በአጠቃላይ ባለሙያውን ለ30 ቀናት ያለዋስትና እንዲታገቱ አድርጓል" የሚሉት አንድ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ግለሰብ ፍርድ ቤቱ የዜጎችን መሠረታዊ የሕግ ከለላ የመጠበቅ እና የዋስትና መብትን የማስከበር ሕገ-መንግሥታዊ ኃላፊነቱን ወደ ጎን በመተው የፖሊስን የተራዘመ የምርመራ ሰበብ በተደጋጋሚ ማስተናገዱ የፍትሕ ሥርዓቱ ለፖለቲካዊ ጫና እና ፍላጎት ተገዥ መሆኑን የሚያሳይ አሳሳቢ ማሳያ ነው ብለዋል።
ፍርድ ቤቱ አሁን ላይ ለሐምሌ 10 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ የሰጠ ሲሆን በዕለቱ የሚሰጠው ውሳኔ በከፍተኛ ሁኔታ ይጠበቃል።
በተያያዘ ዜና ዶ/ር ሀብታሙ አለሙ በቁጥጥር ስር በመዋላቸው ምክንያት ከአቅም በላይ በሆነ የሕግ ጫና ከሥራ ገበታቸው መራቃቸው በግልጽ እየታወቀ የሚሠሩበት የድሬዳዋ ድልጮራ ሪፈራል ሆስፒታል ለሁለተኛ ጊዜ የሥራ ጥሪ ማስታወቂያ ማውጣቱ ተገልጿል።
ይህ ዓይነቱ አሠራር መሠረተ-ቢስና ያልተገባ አስተዳደራዊ ጫና ከመሆኑም በላይ በባለሙያው ላይ የሥራ ዋስትና ስጋት እየፈጠረበት እንደሚገኝ ተጠቁሟል።
"አንድ ዜጋ በሕግ ሂደት ውስጥ ባለበት ወቅት በግዳጅ በተፈጠረ መቅረት ምክንያት ተቋማዊ ጫና ማድረግ በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 20 ንዑስ አንቀጽ 3 ላይ ከተደነገገው "የንጹሕነት ግምት መብት" (Presumption of Innocence) መርህ ጋር ሙሉ በሙሉ የሚጋጭ ተግባር ነው" የሚሉት ሌላኛው ምንጭ ናቸው።
የሥራ ቦታን እንደ ፖለቲካዊ መሣሪያ በመጠቀም በሕክምና ባለሙያው ላይ እየተደረገ ያለው ይህ ድርጊት ስልታዊ በደል መሆኑን የጠቀሱት እነዚህ የመረጃ ምንጮች የድሬዳዋ አስተዳደር የመንግሥት መዋቅሩንና ተቋማትን መሣሪያ በማድረግ በነጻነት ለመወዳደር በሞከረ ንጹሕ ዜጋና የሕዝብ ሕይወት በሚታደግ ባለሙያ ላይ ግልጽ የሙያ ህልውናን የመቅጨት፣ የመበቀልና የማግለል ስልታዊ ዘመቻ ከፍቷል ሲሉ በጽኑ ወቅሰዋል።
ይህን ሕገ-ወጥ እስራትና የተደራጀ አስተዳደራዊ ጫና ለመቋቋም የዶክተሩ ሕጋዊ ተቋማዊ መብት እንዲጠበቅለትና ይህ በግዳጅ መቅረት ምክንያት የሚደረግ መገለል በአስቸኳይ እንዲቆም ለተለያዩ የሰብአዊ መብትና የሙያ ተቋማት ይፋዊ የአቤቱታ ደብዳቤዎች መግባታቸው ታውቋል።
ቤተሰቦቹ ሕጋዊ ከለላ ፍለጋ አቤቱታ ካስገቡባቸው ዋና ዋና ተቋማት መካከል የድሬዳዋ ጤና ቢሮ፣ የድልጮራ ሪፈራል ሆስፒታል አስተዳደር፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) እና የኢትዮጵያ ሕክምና ማኅበር (EMA) ቀዳሚዎቹ ናቸው።
| መሠረት ሚድያ |




መሰረት ሚዲያ ትክክለኛ የህዝብ አለኝታ