"እኔ የምርጫ ደጋፊ ነኝ፣ ምርጫ ፍፁም ዴሞክራሲያዊ በሆነ ሀገር ውስጥ ብቻ የሚደረግ የደስታ ማብሰሪያ ሳይሆን ወደ ዴሞክራሲ ለመሸጋገር የሚደረግ ታላቅ የትግል አውድ ጭምር ነው"
በዞራን አባይ ለመሠረት ሚድያ
(መሠረት ሚድያ)- ምርጫ ፍፁም ዴሞክራሲያዊ በሆነ ሀገር ውስጥ ብቻ የሚደረግ የደስታ ማብሰሪያ ሳይሆን ወደ ዴሞክራሲ ለመሸጋገር የሚደረግ ታላቅ የትግል አውድ ጭምር ነው። ዲሞክራሲም ሆነ ምርጫ በአንድ ጀምበር የሚገነቡ ሳይሆኑ በረጅም ውጣ ውረድ እየታረሙና እየዳበሩ ሚገኙ ሂደቶች ናቸው።
ዲሞክራሲ ሂደት መሆኑን ካመንና ሂደት እንደሚፈልግ ከተገነዘብን ደግሞ በውስጡ ቀስበቀስ እየታረሙ ሚሄዱ ስህተቶች መኖራቸውን ለመቀበል እንገደዳለን።
በአገራችን ወቅታዊ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ "የምርጫው ውጤት አስቀድሞ የሚታወቅ ስለሆነ መምረጥም ሆነ መሳተፍ ፋይዳ የለውም" የሚሉ ድምፆች በተደጋጋሚ ይሰማሉ። ይህ አመለካከት ሊዳብር የቻለበት የበዙ ነባራዊና ታሪካዊ ምክንያቶች ሊኖሩ ቢችሉም ከፖለቲካ ሳይንስና ከታሪክ ተሞክሮ አንጻር ግን የዲሞክራሲ ሂደትን ወደኋላ የሚጎትት እንጂ መፍትሄ የሚያመጣ አካሄድ አይደለም።
በዓለም ታሪክ ውስጥ በአንድ ምርጫ ብቻ ፍጹም ዲሞክራሲን የገነባ አገር የለም። ለአብነት ያህል፣ በዓለማችን የዲሞክራሲ ተምሳሌት ተደርጋ በምትወሰደው አሜሪካ እ.ኤ.አ በ1788 የመጀመሪያውን ምርጫ ካካሄደች በኋላ ሴቶች የመምረጥ መብት ለማግኘት ከ130 ዓመታት በላይ መታገስና መታገል ነበረባቸው። ጥቁር አሜሪካውያን ደግሞ ሙሉ የድምፅ መብታቸውን ያረጋገጡት በ1965 ነው።
ይህ የሚያሳየው ዲሞክራሲ በምርጫ ሂደት ውስጥ እየተሳተፉ፣ ስህተቶችን እያረሙና ተቋማትን እየገነቡ የሚሄዱበት የረጅም ጊዜ ጉዞ መሆኑን ነው። በዚህ መሐል መሳተፍን ማቆም ማለት ጉዞውን ማቆምና ማነቅ ማለት ነው።
እኛ ኢትዮጵያዊያን ምርጫን "አያስፈልግም" በሚያስብል ደረጃ ፈትነንና እስከመጨረሻው ታግለንበት አናውቅም። ፈትነንና ሞክረን ባላየነው ጉዳይ ድምዳሜ መስጠት ደግሞ የራስን ስንፍና በ"ምርጫ አያስፈልግም" ሰበብ ለመሸፈን ሚደረግ ስልታዊ እርምጃ ይሆናል።
በአገራችን የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ምርጫን ከነጉድለቶቹም ቢሆን እንደ ጠንካራ የፖለቲካ ትግል መሳሪያ የመጠቀም ልምዳችን አናሳ ነው። ሆኖም ግን ምርጫን እንደትግል መሳሪያ ለመጠቀም ሙከራ ቢደረግ ምን ሊገኝ እንደሚችል የ1997ቱ አገራዊ ምርጫ ሕያው ምስክር ነው።
በወቅቱ የነበሩ የተቃዋሚ ሃይሎች ( ቅንጅት) በከተሞች ላይ ትኩረት አድርገው በሰሩት ስልታዊና ጠንካራ የቅስቀሳ ስራ፣ ምርጫን እንደ ትልቅ መታገያ መሳሪያ መጠቀም እንደሚቻል በተጨባጭ አሳይተዋል።
ምርጫው በብዙ ውጣ ውረዶች የታጀበ ቢሆንም የህዝብን የለውጥ ፍላጎት ማቀጣጠልና እስከ ዋና ከተማዋ አዲስ አበባን ሙሉ በሙሉ እስከማሸነፍ ደርሰዋል። ያ ክስተት በትክክልም ምርጫ ጥቅም ላይ ከዋለ ምን ያህል ጠንካራ የሰላማዊ ትግል መንገድ እንደሆነ በተግባር ያሳየ ታሪካዊ ክስተት ነበር።
ታዲያ ዛሬም ቢሆን የፖለቲካ ፓርቲዎች በከተሞች ላይ ጠንካራ ስራ በመስራት፣ ታዛቢዎችን በንቃት በመመደብና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ ለእውነተኝነት የቀረበ የምርጫ ሂደት እንዲኖር ጫና መፍጠር ይችላሉ። ይህን ማድረግ ስልጣን ከመያዝ ባለፈም ለሚቀጥለው ትውልድ የሚተርፍ ጠንካራ የዲሞክራሲ መሠረት ጥሎ ማለፍ መሆኑም መዘንጋት የለበትም።
እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገራት ውስጥ የመንግስት ከፍተኛ አመራሮች ዲሞክራሲን ለመተግበርና ሀቀኛ ምርጫ ለማድረግ ቁርጠኛ ቢሆኑ እንኳ ሂደቱን በአንድ ጀምበር ስኬታማ እንዳይሆን የሚያደርጉ በርካታ ተጨባጭ አገራዊ ፈተናዎች አሉ፦
* የኢኮኖሚ ፈተና (ድህነት)፦ የህዝብ መሰረታዊ ፍላጎቶች ባልተሟሉበት ሁኔታ የዲሞክራሲ ተቋማትን በበቂ በጀት መደገፍ ፈታኝ ይሆናል።
*የታችኛው መዋቅር ስነ-ልቦና፦ በታችኛው የመንግስት መዋቅር አካባቢ የሚገኙ አስፈጻሚዎች የፖለቲካ ስልጣንን ከግላዊ ህልውና ጋር የማያያዝ ዝንባሌ አላቸው።
*የማህበረሰብ ንቃተ-ህሊና፦ የዲሞክራሲ ባህልና እሴቶች በማህበረሰቡ ውስጥ ገና እንጭጭ ደረጃ ላይ ይገኛል።
*የተቋማት ደካማነት፦እንደ ምርጫ ቦርድ፣ ፍርድ ቤቶችና የሰብዓዊ መብት ተቋማት ያሉ ገለልተኛ ተቋማት ገና በጠንካራ መሠረት ላይ የቆሙ አይደሉም።
እነዚህን ተግዳሮቶች መፍታት የሚቻለው ግን ከመጫወቻ ሜዳው በመውጣት ሳይሆን፣ በትዕግስትና በአስተዋይነት በመሳተፍ ተቋማቱን በሂደት እንዲጎለምሱ በማገዝ ብቻ ነው።
ፖለቲካ ማለት በመሰረቱ የጋራ ስምምነት (Social Contract) ማለት ነው። ይህ ስምምነት ደግሞ የሚመጣው በመሳተፍ እንጂ በመሸሽ አይደለም።
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ እንዳለው ዜግነት በደም ወይም በትውልድ የሚገኝ ማዕረግ ብቻ ሳይሆን በአገር ጉዳይ ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ የሚገለጽ ተግባር ነው።
ለተከበራችሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ የምመክረው፤ ለአገራችሁ የምታስቡ ከሆነ በፖለቲካዊ ሂደቶች ላይ በንቃት ተሳተፉ። መሳተፍ ማለት ግን መቃወም፣ መዘላለፍ የፓርቲ አመራር ማለት ብቻ አይደለም። ይልቁኑ መብትና ግዴታውን ጠንቅቆ የሚያውቅ፣ የሚደረገውን የፖለቲካ ሂደት የሚረዳና የሚከታተል የነቃ ዜጋ መሆን ማለት ነው።
ዜጋ ከነቃ፣ በምንም ተዓምር የነቃ ማህበረሰብ ያልነቃ ስርዓት አይወልድም። አገሩንና የታሪክ ሂደቱን በሚገባ የሚረዳ ዜጋ፣ በብሄርና በዘር ፖለቲካ ተጠልፎ ከወንድሞቹ ጋር አይጋጭም። የበቃ ዜጋ ሁልጊዜም ለውጥን የሚጀምረው ከራሱ ተሳትፎ ነው፤ ከአገሩ መቀበል ሚፈልገው ቀድሞ ሚሰጠው አሱ እረሱ ነው።
አገር የኔ፣ ያንተና ያንቺ ድምር ውጤት ነው።
መንግስት የኔ፣ ያንተና ያንቺ መስታወት ነው።
ዲሞክራሲ የኔ፣ ያንተና ያንቺ የተሳትፎ ውጤት ነው።
ስለሆነም ዛሬ ባይሆን እንኳ ለውደፊት ለሚደረግ ምርጫ እንደ አንድ ትልቅ የዲሞክራሲ የሂደት እርምጃ በመውሰድ ድምጻችንን በመስጠትና በንቃት በመሳተፍ አገራዊ ግዴታችንን እንወጣ።
ሰላም ለአገራችን!
***መሠረት ሚድያ ላይ የሚቀርቡ አስተያየቶች በሙሉ የፀሀፊዎቹ እንጂ የሚድያው አቋም እንዳልሆኑ ልናስታውስ እንወዳለን።
| መሠረት ሚድያ |





ወዳጄ በፃፉት ሀሣብ እንደ ሀሣብ እስማማለሁ በአንድ ጀምበር እማ የሚለወጥ ነገር የለም! በትግልም አመት እና ምዕተ አመታትንም የሚወስዱ ፅናትን የሚጠይቁ ጉዳዮች አሉ።ለምሣሌ የሀገር ኢኮኖሚያዊ እድገት፣ ከድህነት ለመውጣት የሚደረግ ግላዊ እና ሀገራዊ ልፋት በተለይ ከተስፋ ጋር በህብረት ሲሆን ብዙ መስዋትነት እየተከፈለም ልክ እንደቻይናውያኑ፣ እንደ ጃፓናውያኑ ቁርጥ የለ የመለወጥ ህዝባቸውን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ማንነታቸውን አሣልፈው የሠጡ መሪዎች ባሉበት እርሶም ባነሡዋት አሜሪካ ጭምር መራር የሆኑ ሂደቶችን አይተናል። ነገር ግን ወዳጄ እንደኢትዮጵያ ባሉ እንደኔይቱ ሀገሮች እንደዚህ አይነቱ ተስፋ ያለ አይመስለኝም። በተለይ የግል ስበዕነቸውን እና ምቾታቸውን ብቻ ለመገንባት የሚጥሩ መሪዎች ፣በራሳቸው ጭንቅላት ሣይሆን በጥቅም ፈላጊ አጋር መሣይ ጠላቶች ሀገራቸውን የሚመሩ ፣ የሩቅ ጊዜ ብሔራዊ እቅድ የሌላቸው፣ ሀገሪቱን አንድ ወደፊት ያስኬዱ መስለው ሁለት ሶስት ጊዜ ወደኋላ የሚጎትቱ፣ የአስተሣሠብ ነቀርሳ የመረዛቸው መሪዎች በሚይዟት እና በሚመሯት ሀገር ግን አስቸጋሪ እንደሚሆን ነው። መርጠን እናውቃለን በመሠለን እርሶም እንዳሉት -97ቱም _2014ቱም ከዚያ በፊት በነበሩትም በትግል ጉዞው የራስን አስተዋፅዖ ለማበርከት ፡የዘንድሮው ግን እኮ ምርጫ የሚባል ሳይንስ ውስጥ የሚገባ ሂደት አይደለም። የአንድ ክፍል ተማሪዎች አለቃቸውን ለመምረጥ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ እና የተፎካካሪዎች ግብ ግብ የመራጮች እጅን የማውለብለብ ነፃነትን ያህል የማይሆን ኩነት ነው። አእንደውም የሀገርን ሀብት በይስሙላ እንደማባከን ነው የመሠለኝ። ለታይታ! ማንን ለመምረጥ ልሳተፍ !? ምን አይቼ ድምፄን ለመን ልስጥ ገና ለገና ዲሞክራሲ ሂደት ነው ብዬ የማላውቀውን ድጋፌን ልቸረው? ግራ ገብቶን እኮ ነው? ወይስ እንደልጆች ጨዋታ “አሌ ቡም” ብዬ በጄ ጣቶች ቁጥር ሰጥቼ ባቦሠጡኝ ልመርጥ ነው? የማላውቀውም መለዓክ የማውቀውም ሠይጣን ለኔ ያው ናቸው! ስለዚህ ወዳጄ ሆይ እኔ በዚህ ምርጫ የመረጥኩት ድምፀ ተአቅቦን ነው! ይህም የዲሞክራሲው እድገት አንዱ ማሣያ በመሆኑ!