በአሰኮ ወረዳ እየተፈፀመ ያለውን ጥቃት እንዲያስቆሙ የተላኩ 'ሪጴ ሎላ' የተባሉ የክልሉ የጸጥታ ኃይሎች የሲቪል ዕርዳታ እንዳይገባ መከልከላቸው ተገለ
(መሠረት ሚድያ)- በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ አርሲ ዞን በአሰኮ ወረዳ በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች እና አብያተ ክርስቲያናት ላይ የተሰነዘረውን መጠነ-ሰፊ ጥቃት ተከትሎ የወጡ አዳዲስ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የመንግስት የጸጥታ ኃይሎች በስፍራው ደርሰው ጥቃቱን ከመከላከል ይልቅ ከጦርነቱ ቀጠና ርቀው ድጋፍ ወደ አካባቢው እንዳይገባ መከልከላቸው ተገልጿል።
የወረዳው አስተዳደር በሚዲያ ላይ እየተፈጠረ ያለውን ተፅዕኖ ተከትሎ 'ሪጴ ሎላ' የተባሉ ወደ አንድ መቶ የሚጠጉ የጸጥታ አባላትን ወደ አካባቢው እንዳስገባ አንድ የክልሉ መንግስት የመረጃ ምንጭ ለመሠረት ሚድያ ተናግረዋል።
"እነዚህ ኃይሎች ከጥቃቱ ቀጠና ሃያ አምስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኙት አርባ ቀላ እና ቡርቡጭ በተባሉ አዋሳኝ ቦታዎች ላይ ከወረዳው ካድሬዎች ጋር በሬ በማረድ እስከ ምሽቱ አንድ ሰዓት ድረስ ምንም ዓይነት ወታደራዊ እንቅስቃሴ ሳይያደርጉ ቆይተዋል" በማለት እኚህ ስሜ አይጠቀስ ያሉ የመረጃ ምንጭ ተናግረዋል።
ከዚህም በተጨማሪ ከተያያዥ ደጋማ ክፍሎች ንፁሃን ወገኖችን ለመርዳት የመጡ የክርስቲያን ማህበረሰብ አባላትን እነዚህ የጸጥታ ኃይሎች የተሻለ የጦር መሣሪያ የታጠቁ በመሆኑ በጉልበት መንገዱን በመዝጋት እንዳያልፉ መከልከላቸው በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ስጋትና ጥርጣሬ ፈጥሯል ብለዋል።
ከትናንት በስቲያ ጀምሮ በአሰኮ ወረዳ የተጀመረውና በተደራጀ መልኩ የተሰነዘረው ይህ ጥቃት እስካሁን የአርባ ዘጠኝ ሰዎችን ሕይወት እንደቀጠፈ የታወቀ ቁጥራቸው ከሁለት መቶ ሰማንያ በላይ የሆኑ ንፁሃን ደግሞ ያሉበት ባለመታወቁ ሳይገደሉ አይቀሩም የሚል ከፍተኛ ስጋት አሳድሯል።
ጥቃቱን የፈጸሙት የሸኔ ታጣቂዎች ቀደም ሲልም ጠለታ ገብርኤል በሚባለው አካባቢ ከሰባት ጊዜ በላይ ተመሳሳይ ጥቃቶችን ሰንዝረው የነበረ ቢሆንም የአሁኑን ጥቃት ለየት የሚያደርገው ታጣቂዎቹ ከመርቲ ወረዳ፣ ከፈንታሌ፣ ከከረዩ እና ከኢቱ ተሰባስበው ቁጥራቸው በግምት ሦስት ሺህ የሚጠጋ ኃይል በመፍጠር በአሰኮ ወረዳና አካባቢው ላይ መጠነ-ሰፊ ወረራ መፈጸማቸው መሆኑ ታውቋል።
በዚህም ምክንያት ቢዮ ቀበሌ፣ ጠለታ ገብርኤል፣ ኩፍቴ፣ መዳኃኔዓለም እና አካባቢው ሙሉ በሙሉ የወደሙ ሲሆን፣ ጥቃቱ በአሁኑ ሰዓት በእሬቻ ሚካኤል፣ በሱንቴ ማርያም፣ በሌንጫ ኦዳ፣ በኳስ ድሬ፣ በአርባ ቀላ እና በወራንቡስ አካባቢዎች ተስፋፍቶ ይገኛል።
ታጣቂዎቹ አካባቢውን ሙሉ በሙሉ ከበው ሰው እንኳን እንዳያመልጥ እያደረጉ ጭፍጨፋ እየፈጸሙ መሆኑን ነዋሪዎች በከፍተኛ ድንጋጤ ገልጸዋል።
| መሠረት ሚድያ |



ይሄንን ዜና ለእኛ ብትነግሩን ምን ይጠቅመናል? እኛ እንደው ፈሪ ከሆንን ቆየን። ምንም ስለማናመጣም ሊሆን ይችላል። ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ግን ዜናውን ብታደርሱት የሆነ ጫና መንግሥት ላይ ሊያሳድሩ ይችሉ ይሆናል።