አቶ ክርስቲያን እና አቶ ዮሀንስ ፍርድ ቤት ቀርበው ባለበት ሰዐት አክቲቪስት ስዩም ተሾመ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ሀላፊን ሲያነጋግር እንደነበር ታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- "ክሳችን በፍርድ ቤት እየታየ ባለበት ሁኔታ ስዩም ተሾመ የተባለ ግለሰብ በፍትሕ ሂደቱ ላይ ተፅዕኖ እየፈጠረ ነው፣ ስማችንንም አጥፍቷል" በሚል አቶ ዮሐንስ ቧያሌው እና አቶ ክርስቲያን ታደለ ለፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት አቤቱታ ማቅረባቸውን በተደጋጋሚ መዘገባችን ይታወሳል።
የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ተከትሎ የፌደራል ፖሊስ ግለሰቡን ማቅረብ እንደማይችል መናገሩን ባሳለፍነው ሳምንት ዘግበናል።
ችሎቱ "የፌደራል ፖሊስ ግለሰቡን ማቅረብ አልችልም ካለ በቀጣይ ምን ማድረግ አለበት?" የሚለውን ብይን ለመስጠት በትናንትናው ዕለት ቀጠሮ ይዞ ችሎት ተሰይሞ እንደነበር መሠረት ሚድያ የደረሰው መረጃ ይጠቁማል።
በተመሳሳይ ቀን እና ሰዓት ደግሞ ስዩም የተባለው ግለሰብ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ወይዘሮ ሌሊሴ ደሳለኝ እና የእነ አቶ ዮሐንስ ቧያሌውን ክስ የያዘው አቃቤ ሕግ ባለሙያ ጋር በመሆን ከተነጋገሩ በኋላ ወደ ቤቱ መመለሱ ታውቋል።
ይህንኑ ተከትሎ ዛሬ በዋለው ችሎት አቶ ዮሐንስ ቧያሌው "የአገሪቱን የፍትሕ ሥርዓት በተለይ ዳኞችን በአደባባይ ሲዘልፍ የሚውልን ግለሰብ የፌደራል ፖሊስ እና አስፈፃሚው አካል ማቅረብ አልቻልንም በሚል በድርጊቱ እንዲገፋበት ሲያበረታቱት አዝነን ነበር" ብለዋል።
አክለውም "ነገር ግን የዳኞችን ክብር እና የፍትሕ ሥርዓቱን ታማዕኒነት ማስጠበቅ የሚገባው የከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ወይዘሮ ሌሊሴ ደሳለኝ በሕግ የሚፈለግን ሠው በችሎቱ ግቢ ውስጥ አግኝተው አባብለው ሲሸኙት ከዚህ በላይ ምን የሚያሳዝን አለ?" ሲሉ በችሎቱ ቆመው ተናግረዋል።
አቶ ዮሐንስ አክለውም "ይሄ ችሎት ስዩምን እንዴት ማቅረብ እንዳለበት ሲያስብ ሲጨነቅ፣ አለቃችሁ ደግሞ ደጅ ላይ ከግለሰቡ ጋር ሻይ ቡና እያሉ ነበር። እናንተም ከዚህ በላይ ብትሄዱ እንደ እኛ ታስራችሁ ቤተሰባችሁ ሊበተን ስለሚችል ብዙ አናስቸግራችሁም፣ ተውት" ብለዋል።
አቶ ክርስቲያን ታደለ በበኩላቸው "ትናንት ወደ ችሎት ስገባ ስዩምን አይቸው ነበር። ምናልባት የቀረበበትን ክስ ቀርቦ ሊከላከል መስሎኝ ነበር፣ በኋላ ግን በችሎቱ እንዳልተገኘ እና ለመጨረሻ ጊዜ የፌደራል ፖሊስ ጥረት አድርጎ እንዲያቀርበው ትዕዛዝ ሲፅፍ ግለሰቡ ከዚህ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት እና ክሳችንን ከያዘው አቃቤ ሕግ ጋር ተነጋግረው በግቢው መዝናኛ ሻይ ቡና ተገባብዘው መሄዳቸውን ሰማን። እኔ በግሌ ስዩምን አመሰግነዋለሁ፣ የራሴ የሚለውን የመንግሥት ሥርዓት እና የፍትሕ ተቋማትን ልፍስፍስነት ራቁታቸውን አስቀርቷቸዋል" ሲሉ ለችሎቱ ተናግረዋል።
የሁለቱን ተከሳሾች አቤቱታ በፀጥታ የተከታተለው ችሎት በጉዳዩ ላይ አስተያየት ሳይሰጥ የፌደራል ፖሊስ ለመጨረሻ ጊዜ ጥረት አድርጎ ስዩም ተሾመን እንዲያቀርብ ሲል ትዕዛዝ አስተላልፏል።
መረጃን ከመሠረት!




ህግ የለም መፍትሄዉ መግጠም ብቻ ነዉ ይሄ ስርአትን በምንም አጋጣሚ መፋለም ፅድቅ ነዉ ብዬ አምናለሁ በግሌ ምክንያቱም ፀረ ህዝብ ነዉ የህዝብ በሽታም ነዉ ልለዉ እችላለሁ ይቅርታ ለቃሉና
ay hager 😭😭😭