ከሦስት ዓመታት የእስር ቆይታ በኋላ ዛሬ በዋስ ተፈትቶ የነበረው ዶ/ር ሲሳይ አውግቼው ማረሚያ ቤት በር ላይ በድጋሜ ታሰረ
(መሠረት ሚድያ)- በአማራ ክልል ከተከሰተው የፖለቲካ አለመረጋጋት ጋር ተያይዞ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከተያዙ የፖለቲካ እስረኞች መሀል ዶ/ር ሲሳይ አውግቼው ይገኝበታል።
ለሦስት ዓመታት ያህል በእስር ላይ የቆየው ዶ/ር ሲሳይ በዛሬው ዕለት በዋስ ተፈትቶ ከእስር ቤት ሲወጣ በድጋሜ መታሰሩን መሠረት ሚድያ ከቤተሰብ እና ከማረሚያ ቤት ምንጮቹ አረጋግጧል።
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ የፀረ-ሽብር ወንጀል እና የሕገ-መንግሥት አንደኛ ምድብ ችሎት ዶ/ር ሲሳይ በመቶ ሺህ ብር ዋስ እንዲወጣ ብይን መስጠቱን ተከትሎ በዛሬው ዕለት ከቂሊንጦ ማረፊያ ማእከል ተፈትቶ ሲወጣ የፌደራል ፖሊስ በር ላይ ጠልፎ እንደወሰደው ታውቋል።
እስር ቤት በር ላይ ሲጠባበቁ የነበሩ ወዳጅ ዘመዶቹ በፌደራል ፖሊስ መዋከባቸው እና በርካታ የታጠቀ የመንግሥት ኃይል መንገድ ዘግቶ ዶ/ር ሲሳይን ከእስር እስኪወጣ እየተጠባበቀ እንደነበርም ሚድያችን ሰምቷል።
ቀደም ሲል በተመሳሳይ ወንጀል ተጠርጥረው ፍርድ ቤት በዋስ እንዲወጡ ብይን ከሰጠ በኋላ የፌደራል ፖሊስ፣ የፍትሕ ሚኒስቴር ዓቃቤያን ሕግ እና የብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት አባላት በጋራ ሆነው ቂሊንጦ እስር ቤት በር ላይ በመጠበቅ በርካታ ዜጎችን አስረው መወሰዳቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
-መሠረት ሚድያ-



ስርዓት አልበኝነት የነገሰባት ሀገር ናት። ያሳዝናል አሁን በዚህ ስዓት የሁሉም ሰው ዋስ ጠበቃ መድሃኔ ዓለም ብቻ ነው።
አገር በከንቱ ፍጡሮች እየተመራች እንደሆነ ከዚህ በላይ ምንም ማስረጃ አያስፈልግም