ጎሀፅዮን አቅራቢያ ታጣቂዎች 9 ሰአት የፈጀ ጥቃት አድርሰው በርካቶችን እንደገደሉ ታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ጎሀፅዮን ከተማ አቅራቢያ ታጣቂዎች ቅዳሜ ምሽት ለእሁድ አጥቢያ በፈፀሙት ረጅም ሰአት የፈጀ ጥቃት በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰላማዊ ዜጎች እንደተገደሉ ለሚድያችን ከስፍራው እየደረሰ ያለ መረጃ ያሳያል።
ግርሚ ጎባ ወረዳ፣ ልዩ ስሙ አጋምሳ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ በእለቱ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት (መንግስት ኦነግ ሸኔ ብሎ የሚጠራው) አባላት ፈፅመውታል በተባለው በዚህ ብሄር ተኮር ጥቃት እስካሁን የ14 ሰዎች አስስከሬን እንደተገኘ መሠረት ሚድያ ከስፍራው ያሰባሰበው መረጃ ያሳያል፣ በተጨማሪም በርካታ ቤቶች በእሳት ተያይዘዋል።
"ታጣቂዎቹ ከለሊት 9 ሰአት ጀምሮ እስከ ቀኑ 6 ሰአት በነፃነት እየተዟዟሩ ግድያውን እና ቤት ማቃጠሉን ፈፅመዋል" ያሉን አንድ የአካባቢው ነዋሪ ጥቃቱ የአማራ ተወላጆች ላይ ያነጣጠረ ነበር ብለዋል።
"ዘጠኝ ሰአት ሙሉ ስንገደል እና ስንቃጠል የደረሰልን የመንግስት ሀይል የለም። ወንድሞቼን ጨምሮ 14 ሰው ሬሳቸው ተገኝቷል፣ ገና በርካታ ያልተነሳ እና ገደል የገባ ሰው አለ፣ ሲኦል የሆነ ግዜ አሳልፈናል" ብለዋል።
በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች መንደራቸውን ጥለው ተሰደው አሁን ላይ ወይ በጫካ ወይም በፍልቅልቅ ከተማ እና በጎሀፅዮን ከተሞች ባለ አንድ ቦታ ተጠልለው እንደሚገኙ ታውቋል።
በዚሁ አካባቢ ከ2012 ዓ/ም ጀምሮ በርካታ ተመሳሳይ ጥቃቶች ሲፈፀሙ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን የትናንት በስቲያ ምሽቱ ጥቃት ግን በአይነቱም ሆነ በመጠኑ ከፍተኛው እንደሆነ የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።
"ከሟቾቹ በላይ ገደል ውስጥ የገባው ብዙ ነው፣ ወይ አካለ ጎዶሎ ሆኗል፣ ወይ ያለበት ሁኔታ አይታወቁም" ያሉ ሌላኛው ነዋሪ በህይወታቸው ይህን ያህል ጥቃት ሲፈፀም አይተው እንደማያውቁ እና እርሳቸውም በተአምር እንደተረፉ አስረድተዋል።
በዚህ ጥቃት ዙርያ እስካሁን ከኦሮሚያ ክልል ኮሚኒኬሽን ቢሮም ሆነ በመንግስት ሚድያዎች የተባለ ነገር የለም።
መረጃን ከመሠረት!




አመመኝ አመመኝ የወገኔ ሲቃይ፣
ሰው በሀገሩ ላይ ሲሆን ተፈናቃይ፣
እንደዚች ሀገር ህዝብ የት አለ ተበዳይ፣
በሀገሩ መንግስት ሚገደል ሚሳደድ የሚቀበል ሲቃይ።
የት አለ አምላካችን? የት አለ ሁሉን ቻይ?
አይቶ የሚፋረድ የደረሰብንን መከራና ሲቃይ፣ በአምሳሉ ለፈጠረው የሚሆን ተበቃይ።
😭