የፌደራል ፖሊስ ብዙ ጥረት አድርጎ ማግኘት እንዳልቻለ የገለፀው ግለሰብ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በነበረ ውይይት ላይ መገኘቱ መነጋገርያ ሆኗል
(መሠረት ሚድያ)- ሚድያችን ከሰሞኑ በተከታታይ ሲያቀርባቸው በነበሩ ዘገባዎቹ የፌደራል ፖሊስ ለፍርድ ቤት በፃፈው ደብዳቤ አክቲቪስት ስዩም ተሾመ የተባለ ግለሰብን ፈልጎ ማግኘት እንዳልቻለ መግለፁ ይታወሳል።
አክቲቪስቱ በሕግ ቁጥጥር ስር ሆነን ሳለ ስማችንን በማጥፋት ብሎም በፍርድ ቤቱ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እየፈጠረ ነው በሚል አቶ ዮሐንስ ቧያሌውና አቶ ክርስቲያን ታደለ ለከፍተኛ ፍርድ ቤት ማመልከታቸው ይታወቃል።
ፍርድ ቤቱ ስዩም ተሾመን የፌደራል ፖሊስ ይዞ እንዲያቀርበው አራት ጊዜ ትዕዛዝ የፃፈ ቢሆንም ፖሊስ ግለሰቡን ማግኘት አልቻልኩም የሚል ምላሽ እስከዛሬ ሲሰጥ ቆይቷል።
አክቲቪስቱ ግን በዛሬው እለት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሚዲያ ተወካዮች ጋር ባደረጉት አንድ ውይይት ላይ ተገኝቶ እንደነበር የመንግስት ሚድያዎች ያወጧቸው ምስሎች ያሳያሉ።
"ይህ መንግስት ለህግ መከበር ያለውን አተያይ በከፊልም ቢሆን ያሳየ ነው። ህግ ሲጣስ እና የፖሊስ መዋቅር የፖለቲካ ጨዋታ አካል ሲሆን ህዝብም ለህግ ያለው አመለካከት ላይ ጥርጣሬ ያሳድራል" በማለት አስተያየት አንድ የህግ ባለሙያ ናቸው።
"አሳፋሪ ክስተቱን ለመደበቅ እንኳን አልተሞከረም። ግለሰቡ ዳኞችን ጭምር ሲሳደብ የነበረ ነው። ለህዝብ መልዕክቱ 'እኔስ ለምን በህግ እዳኛለሁ? ለምን ህግ ይጠይቀኛል?' የሚል ይመስለኛል" በማለት ለመሠረት ሚድያ ተናግረዋል።
አቶ ዮሐንስ ቧያሌው በወቅቱ "የፍትሕ ሥርዓቱ ጨርሶ እንዲሞት ያደረገው ስዩም ተሾመ ሳይሆን በእሱ ጀርባ ያሉት የመንግሥት ተቋማት ናቸው" ብለው ነበር።
አቶ ክርስቲያን ታደለ ደግሞ "ስዩምን ማቅረብ ያልቻለ የፌደራል ፖሊስ ማረሚያ ቤት ሰብሮ ገብቶ ቁሙ ተነሱ ሲለን ያድራል። የራሳቸውን መንግሥት ሥርዓት እንኳ ማክበር አልቻሉም። የፍትሕ ሥርዓቱ አንድ ጊዜ ሞቷል። ቢያንስ ለእናንተ ለዳኞች ክብር እንኳ ሲባል አዲስ አበባ ተቀምጦ ሲሰድባችሁ የሚውልን ግለሰብ ማቅረብ ነበረበት። ከእኛ ይልቅ የምታሳዝኑኝ እናንተ ናችሁ፣ የሚሰድባችሁን ግለሰብ እንኳ ማቅረብ የሚችል ፖሊስ የለም" ብለው ተናግረው ነበር።
መረጃን ከመሠረት!




ታዲያ በሰላም ታገሉ ማለት ለብጥ አይደለም ነው ምትሉኝ?
ታዲያ ጠብ መንጃ ማንሳት ስህተት ነው ነው እምትሉኝ?