የልጁን እናት በአሰቃቂ ሁኔታ ከገደለ በኋላ ሬሳዋን ቪድዮ በመቅረፅ ለቤተሰቦቿ የላከው ግለሰብ እስካሁን ቲክቶክ በነፃነት እንደሚጠቀም ታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- የደቡብ ወሎዋ መሃል ሳይንት ወረዳ በቅርቡ አንዲት ልጇን በሞት ተነጥቃለች። አለሚቱ ሸጋው የተባለችው ወጣት ለተሻለ ህይወት እና ለደካማ ወላጆቿ ደራሽ ለመሆን ወደ አዲስ አበባ ብቅ ብላ በአንድ ሆቴል ውስጥ የወጥ ቤት ረዳት በመሆን ትሰራ ነበር።
የህይወት ጉዞዋ ግን አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ አየር ጤና አካባቢ በሚገኝ በአንድ ሆቴል ውስጥ በጭካኔ ተቋጭቷል። ወንጀሉን የታዘቡ ደግሞ ይህ ወንጀል የተፈጸመው በታቀደ እና አስቀድሞ በተዘጋጀበት ሁኔታ መሆኑ ደግሞ ድርጊቱን ይበልጥ ዘግናኝ ያደርገዋል ይላሉ።
ተጠርጣሪ ገዳይ ተብሎ ለሚድያችን የተጠቆመው ደሳለኝ ሽመልስ የተባለ ግለሰብ ሲሆን ሚያዝያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም. ከሚሰራበት አሶሳ ከተማ በአውሮፕላን ተሳፍሮ አዲስ አበባ ገብቶ ነበር።
ቅዳሜና እሁድን ከአለሚቱ ጋር አብሮ ካሳለፈ በኋላ፣ እሁድ ለሰኞ አጥቢያ በነበረው ሌሊት አየር ጤና በሚገኘው አሚኒ ሆቴል ውስጥ ህይወቷን ቀጥፎ መሰወሩን የአካባቢው ምንጮች ለመሠረት ሚድያ ተናገረዋል።
ሰኞ ሚያዝያ 12 ቀን ከጧቱ አራት ሰዓት ላይ ፖሊስ የሆቴሉን ክፍል ሰብሮ ሲገባ አስከሬኗን ያገኘ ሲሆን ወዲያውኑም ለምርመራ ወደ ዳግማዊ ሚኒሊክ ሆስፒታል እንዲወሰድ ተደርጓል።
የአለሚቱ ቤተሰቦች ሀዘን ግን በዚህ ብቻ የሚያበቃ አልነበረም።
ከሁለት ዓመት በፊት ሌላ ወንድ ልጃቸውን በሰው እጅ በግፍ ተነጥቀው የነበሩት እነዚህ አቅመ ደካማ ወላጆች፣ ዛሬ ደግሞ የዓይን ብሌናቸውን አለሚቱን አጥተው በከፍተኛ መሪር ሀዘን ውስጥ እንደሚገኙ ታውቋል።
ተጠርጣሪው ደሳለኝ ሽመልስ ወንጀሉን ፈጽሞ ከጠፋ በኋላ ለሟች አጎት ማስፈራሪያ አዘል የአጭር የፅሁፍ መልዕክት በስልኩ የላከ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በአሶሳ ከተማ በነፃነት እየተዝናና መሆኑን የሚያሳዩ የቲክቶክ ቪዲዮዎችን በመልቀቅ በቤተሰቡ ቁስል ላይ እንጨት እየሰደደ እንደሚገኝም ታውቋል።
"ዳታ ክፈትና እያት እንዴት እንዳረግኳት" በማለት ለቤተሰብ አባል መልዕክት መላኩንም ለሚድያችን ተናግረዋል። መሠረት ሚድያ ይህን ቪድዮ የተመለከተ ሲሆን በዘግናኝነቱ ምክንያት በቀጥታ ላለማቅረብ ወስኗል።
"የትውልድ ቦታው ምስራቅ ጎጃም መርጦ ለማርያም ዲቦ የተባለ ስፍራ የሆነው ይህ ግለሰብ ለህግ ሳይቀርብ መቆየቱ የቤተሰቡን ስቃይ አባብሶታል" ያሉት አንድ ቤተሰቡን የሚያውቁ ግለሰብ ናቸው።
በአሁኑ ወቅት የአለሚቱ አስከሬን በትውልድ ቦታዋ መሃል ሳይንት ወረዳ ሚያዝያ 14 ቀን በክብር ቢያርፍም ተጠርጣሪው ግን በቲክቶክ ማህበራዊ ገፅ ላይ በነፃነት እየታየ ይገኛል።
ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተልላቸው እና ድምፅ የሚሆናቸው ጠንካራ ሰው ያጡት እነዚህ ወላጆች የህግ ያለህ እያሉ ይማጸናሉ።
"ፖሊስ እና የሚመለከታቸው የፍትህ አካላት ይህን ግለሰብ ከአሶሳ አድነው ለህግ እንዲያቀርቡ እና ለዚህ ምስኪን ቤተሰብ ፍትህ እንዲሰፍን መጠየቅ የሁላችንም ሰብዓዊ ግዴታ ነው" የሚሉት አስተያየት ሰጪዎች ግለሰቡ አሁን ሌሎች የቤተሰቡን አባላት ለመግደል እየዛተ ነው ይላሉ።
| መሠረት ሚድያ |









