በትግራይ ክልል ባለፈው አንድ ወር ውስጥ ብቻ ሰላሳ ሺህ ወጣቶች በግዴታ ታፍሰው ለውትድርና መወሰዳቸው ተሰማ
(መሠረት ሚድያ)- ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በትግራይ ክልል ውስጥ የተጀመረው መጠነ ሰፊ እና አስገዳጅ የወጣቶች ወታደራዊ አፈሳ በህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ዋነኛ አስፈጻሚነት ተባብሶ መቀጠሉን ከክልሉ ለሚድያችን የደረሱ መረጃዎች ጠቁመዋል።
ለደህንነታችን ሲባል ስማችን አይጠቀስ ያሉ የክልሉ ምንጮች ለመሠረት ሚድያ ይፋ ባደረጉት መረጃ መሰረት ይህንን የኃይል እርምጃ በመቃወም እና ከአፈሳው ለማምለጥ የሞከሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን ከአስር በላይ የሚሆኑት ደግሞ በፀጥታ ኃይሎች በተተኮሰ ጥይት ለህልፈትና ለከባድ የአካል ጉዳት መዳረጋቸውን አረጋግጠዋል።
ድርጊቱን በቅርበት የሚከታተሉ ወገኖች እንደገለጹት ይህ አይነቱ ሰውን አስገድዶ ወደ ውትድርና ማስገባትና ለህልፈት መዳረግ ዓለም አቀፍ የጦር ወንጀል ተብሎ ሊፈረጅ የሚችል እጅግ አደገኛ ተግባር ነው።
ይህንን አሳሳቢ የግዳጅ ምልመላ አስመልክቶ አስተያየታቸውን የሰጡት የትግራይ ምሁርና የማህበራዊ ሚዲያ ተፅዕኖ ፈጣሪ ሸዊት ውዳሴ እንደገለጹት ህወሓት የትግራይን ወጣቶች በማስፈራራትና በማስገደድ ወደ ታጠቀው ወታደራዊ ኃይል እያሰገባቸው ሲሆን ይህ ድርጊት ከፍተኛ የሆነ የሰብአዊ መብት ረገጣ ከመሆኑም በላይ የአንድን ሙሉ ትውልድ መጻኢ ዕድልና የወደፊት ተስፋ በቀጥታ አደጋ ላይ የሚጥል ጥቃት ነው።
በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶችም በጉዳዩ ላይ ያላቸውን ከፍተኛ ተቃውሞ እያሰሙ ሲሆን የሳልሳይ ወያነ ትግራይ ፓርቲ በቅርቡ ባወጣው መግለጫ ህወሓት ከጥቂት ቀናት ወዲህ እያካሄደ ያለው አስገዳጅ የወጣቶች ወታደራዊ አፈሳ ህዝብን ከፍተኛ ጭንቅና ስነ ልቦናዊ ቀውስ ውስጥ የከተተ በመሆኑ በአስቸኳይ እንዲቆም ጥሪ አቅርቧል።
ሳልሳይ ወያነ አክሎም እየተካሄደ ነው ያለውን አስገዳጅ አፈሳ ለማስቆም አስፈላጊ የሆኑትን የፖለቲካዊና የዲፕሎማሲያዊ ሥራዎችን በሙሉ በቁርጠኝነት እንደሚሠራ አስታውቋል።
የክልሉን ወቅታዊ ሁኔታና የህዝቡን እንግልት ያብራራው ይህ የፖለቲካ ፓርቲ የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግስት በጦርነቱ ምክንያት የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ ቀደመ ቀያቸው በአስቸኳይ እንዲመልስ የጠየቀ ሲሆን በትግራይ ክልል ላይ ደመወዝና መሰረታዊ የሆኑ የፍጆታ ሸቀጦችን መከልከል ፍጹም ተገቢነት የሌለው ተግባር በመሆኑ በፅኑ እንደሚቃወመው በይፋ ገልጿል።
በተጨማሪም ህወሓት በቅርቡ "መልሻለሁ" ላለው የክልሉ ምክር ቤት እውቅና እንደማይሰጥ የገለጸው ሳልሳይ ወያነ ምክር ቤቱ የሚያሳልፋቸው ማናቸውም ውሳኔዎች በህዝቡና በሌሎች አካላት ዘንድ ምንም አይነት ተቀባይነት የሌላቸው መሆኑን በግልጽ አሳውቋል።
ፓርቲው በትግራይ ነፃነት ፓርቲ አመራሮች መካከል በቅርቡ በተፈጠረው የመሰንጠቅና የአለመግባባት አደጋ ምክንያት ከፓርቲው ጋር ፈጥሮት የነበረውን የግንባር ምስረታ ለጊዜው ማቋረጡን ይፋ ያደረገ ሲሆን በትግራይ ውስጥ ሌላ ዙር አውዳሚ ጦርነት እንዳይከሰት በትግራይ ተወላጆች መካከል አስቸኳይ ውይይትና እርቅ እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።
አገር በቀል የሲቪክ ማህበራትም በትግራይ ክልል ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ የምርመራ ውጤቶችን እያወጡ ሲሆን ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች ኢትዮጵያ የተባለው ድርጅት ለጀርመን ድምጽ በሰጠው ቃል በክልሉ መጠነ ሰፊ የግዳጅ አፈሳ እየተደረገ መሆኑን በተጨባጭ አረጋግጧል።
የመብት ድርጅቱ በጉዳዩ ላይ እያደረገ ያለውን ዝርዝር የምርመራ ውጤት በቅርቡ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ይፋ እንደሚያደርግ የጠቆመ ሲሆን የደረሱት መረጃዎች እንደሚያመለክቱት አፈሳው በዋናነት ያነጣጠረው ቀደም ሲል ከውትድርና ተቀንሰው በተመለሱ ታጣቂዎች፣ በቤተሰብ ደረጃ ወደ ትግሉ አንድም ሰው ባላስገቡ ወገኖች እና ወጣቶች በብዛት በሚገኙባቸው እንደ ወርቅ ማውጫ አካባቢዎች ላይ መሆኑን ጠቅሷል።
ድርጅቱ እንደገለጸው የዚህ አስገዳጅ ተግባር መነሻ ምክንያት በአገሪቱ ካለው ውስብስብ ፖለቲካዊ ኹኔታ ጋር በቀጥታ የሚገናኝ ሲሆን በተለይም የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ወደ መፍረስ ደረጃ መድረሱና በክልሉ የተፈጠረው የፀጥታ ስጋት ዋነኛው መንስኤ መሆኑን አስታውቋል።
| መሠረት ሚድያ |



