ናይሮቢ ውስጥ ህይወቱ አልፎ የተገኘው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች እና ጋዜጠኛ ያዕቆብ ያታኔ ተከታታይ ማስፈራሪያዎች ይደርሱት እንደነበር ታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- ኬንያ ውስጥ ረዘም ላለ ግዜ ይኖር የነበረው እና እንደ ዛራ ሚድያ፣ አዲስ ስታንዳርድ ላሉ ሚድያዎች በመፃፍ የሚታወቀው ያዕቆብ ያታኔ ከስድስት ቀን በፊት የሚኖርበት ክፍል ውስጥ ህይወቱ አልፎ መገኘቱ ታውቋል።
ያዕቆብ በስደት ወደ ኬንያ ካቀና በኋላ ተወልዶ ባደገበት የኮንሶ አካባቢ ያለውን የመልካም አስተዳደር ችግር እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት በማጋለጥ ይታወቃል፣ እስከ ህልፈቱ ድረስም በሚድያዎች እና በማህበራዊ ሚድያ ይህን ሲያደርግ እንደነበር ተመልክተናል።
አንድ ሟቹን የሚያውቅ ግለሰብ ለመሠረት ሚድያ እንደጠቆመው ያዕቆብ ከመሞቱ ጥቂት ወራት በፊት ማስፈራሪያዎች ይደርሱት እንደነበረው እንደነገረው ተናግሯል።
"ክትትል እየተደረገበት እንዳለ ነግሮኝ ነበር፣ በተለይ ከመንግስት ጋር ግንኙነት ያላቸው ሰዎች ይከታተሉት እንደነበር ስጋቱን ነግሮኛል። እንደውም አንድ ስክሪንሾት በወቅቱ ልኮልኝ ነበር" በማለት ይህን ጋዜጠኛው በወቅቱ የላከለትን ምስል ለሚድያችን አጋርቷል (ከታች ይታያል)።
መሠረት ሚድያ እንዳረገጋገጠው አለም አቀፉ ከጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ሲ ፒ ጄ ጉዳዩ ላይ በጋዜጠኛው ህልፈት ዙርያ ማጣራት ጀምሯል።
ግለሰቡ ህይወቱ መረጃውን ቀድሞ ያጋራው 'WT Media' እንደዘገበው የያዕቆብ ያታኔ የሞት ምክንያት መርዝ እና አካላዊ ጥቃት ሊሆን እንደሚችል የሚያሳዩ የሕክምና ማስረጃዎች ተገኝተዋል።
ሚድያው አክሎም ከወራት በፊት የደረሰበትን ማስፈራራት ተከትሎ ጉዳዩን ለኬንያ ፖሊስና ለተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) ቢያሳውቅም፣ አስተማማኝ ጥበቃ ሳያገኝ ቆይቷል ብሏል።
"በናይሮቢ ሲቲ ሞርቹሪ (City Mortuary) የተደረገው የመጀመሪያ ደረጃ የአስከሬን ምርመራ ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ የጋዜጠኛው ሞት በህክምና ቋንቋ DIC (Disseminated Intravascular Coagulation) በሚባል ሁኔታ የተከሰተ እንደሆነ WT Media ተመልክቷል" ብሎ መረጃ ያጋራው ሚድያው ይህ የጤና መታወክ ብዙውን ጊዜ የሚከሰተው በከፍተኛ ኢንፌክሽን ወይም በሰውነት ውስጥ በሚሰራጭ መርዝ (Toxins/Poisoning) ምክንያት እንደሆነ የሕክምና ባለሙያዎች ይገልጻሉ ብሏል።
አክሎም "ምርመራው በተጨማሪ በጋዜጠኛው የጭንቅላት ቆዳ ስር የደም መፍሰስ (Parietal scalp contusion) እና በሁለቱም ሳንባዎቹ ላይ የደም መፍሰስ (Bilateral lung haemorrhage) መኖሩን አረጋግጧል" በማለት መረጃ አጋርቷል።
ጋዜጠኛ ያዕቆብ ያታኔ ከኮንሶ ማህበረሰብ የተገኘ ምሁር ሲሆን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ውስጥ በእንግሊዝኛ ፕሮግራም ኤዲተርና ዘጋቢነት ለረጅም ጊዜ ከማገልገሉ በላይ በዩኒቨርሲቲ መምህርነትና ተመራማሪነት እንዲሁም በተለያዩ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች (NGOs) በከፍተኛ ኃላፊነት ሰርቶ ነበር።
-መሠረት ሚድያ-



