የቦሌ ቡልቡላ አካባቢ የልማት ተነሺ አርሶ አደሮች 'እጅግ አነስተኛ' የተባለ ካሳ ወስዳችሁ ቦታውን ለማህበር ቤቶች ልቀቁ መባላቸውን ለመሠረት ሚድያ ተናገሩ
(መሠረት ሚድያ)- የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ልዩ ስሙ ቦሌ ቡልቡላ ኦሾ አንድ እና ሁለት እንዲሁም ወረገኑ በተባሉ አካባቢዎች ለልማት በሚል ለአርሶ አደር ገበሬዎች የሚሰጠው የካሳ ክፍያ እጅግ አነስተኛ መሆኑ በነዋሪዎች ላይ ከፍተኛ ቅሬታና ጭንቀት ፈጥሯል።
ለአየር መንገድ ጀርባ ቅርብ በሆነው በዚህ ሰፊ የእርሻ መሬት ላይ ከቦሌ ቡልቡላ እስከ ኮዬ ፈጬ አዲሱ መንገድ (በተለምዶ ፍልውሃ) ድረስ ያሉ ማሳዎችና የግጦሽ መሬቶች ለመምህራን እና ለጤና ባለሙያዎች የመኖሪያ ቤት መስሪያ እንዲሆኑ ተለይተዋል።
ይሁን እንጂ የቦሌ ክፍለ ከተማና የወረዳ 12 አመራሮች ነዋሪዎችን ሰብስበው “አንድ ካሬ ሜትር በ2,000 ወይም በ1,000 ብር፣ ሌላው ቀርቶ በ2014 ዓ.ም በወጣ አሮጌ ህግ ለአንድ ካሬ ሜትር 770 ብር ብቻ እየተሰላችሁ በሁለት ሺህ ካሬ አራት ሚሊዮን ብር ወስዳችሁ ልቀቁ” ማለታቸውን ተነሺዎቹ በምሬት ይናገራሉ።
የአካባቢው አርሶ አደሮች “እኛ ልማት አንጠላም፤ ነገር ግን በዚህ ዘመን በአራት ሚሊዮን ብር ምን እናደርጋለን?” ሲሉ ይጠይቃሉ።
በአሁኑ ወቅት ለመምህራን በቦታው ላይ ግንባታ የተጀመረ ሲሆን የሐኪሞች ፕሮጀክትም በተመሳሳይ መልኩ በይፋ በመጪው ቅዳሜ ሊጀመር መሆኑ በገበሬው ዘንድ ያለውን የዋስትና ማጣት ስጋት ይበልጥ አጉልቶታል።
የከተማ አስተዳደሩ ቀደም ሲል ከሪል እስቴት አልሚዎችና ከግል ባለሀብቶች ጋር በመሆን የ70/30 የህዝብና የግል አጋርነት (PPP) የቤት ልማት ፖሊሲን ተግባራዊ ሲያደርግ መቆየቱ ይታወቃል። በዚህ አሰራር መሰረት አልሚዎች 70 በመቶውን ለገበያ አቅርበው 30 በመቶውን ለዝቅተኛው ማህበረሰብና ለከተማው መስተዳድር ያስረክባሉ።
ይህንን ተሞክሮ ያነሱት የአካባቢው ገበሬዎች “ከዚህ በፊት የከተማ ግብርና ተብለን ተዘናግተናል፤ አሁን ግን የምንፈልገው 70/30 እንዲደረግልን ነው፤ ከሚሰራው ህንፃ 30 ፐርሰንት ተሰጥቶን የልጆቻችንና የልጅ ልጆቻችን ህይወት መቃኛ እንዲሆን እንሻለን” በማለት የዘላቂ መብት ጥያቄያቸውን ያቀርባሉ።
ገበሬዎቹ በአሁኑ ወቅት ምንም አይነት የገንዘብ ክፍያም ሆነ የጽሁፍ መተማመኛ ሰነድ ሳይሰጣቸው ማሳቸውን እንዲለቁ መገደዳቸውን ይገልጻሉ።
“እኛ ገበሬዎች ነን፤ እርሻችን ከለላችን ነው፤ እርሻም የለም፣ ብርም የለም፣ መተማመኛም በሌለበት ሁኔታ በምን እንኖራለን?” ሲሉ በጭንቀት ይናገራሉ።
በተያያዘም የክፍለ ከተማው አመራሮች የገበሬውን አቤቱታና ቅሬታ ለአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከማድረስ ይልቅ እያፈኑት እንደሆነና መጪው የቅዳሜ ፕሮግራም ሳይደርስ እልባት እንዲሰጠው አደራ ብለዋል።
ነዋሪዎቹ ሲያጠቃልሉም “አሁን ካለው የኑሮ ውድነት አንጻር የተመደበው ብር ተስፋ ሰጪ ባይሆንም ቢያንስ ለገበሬው ቋሚ ንብረትና ዋስትና ሊሰጠው ይገባል፤ ያለበለዚያ ግን የልጅ ልጆቻችን የት ይሂዱ? ወይስ ለማኝ ይሁኑ?” ሲሉ ለሚመለከተው አካል ድምጻቸውን በሚድያችን በኩል አሰምተዋል።
| መሠረት ሚድያ |



