በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ ሶስት ወጣቶች 'ፋኖ ናችሁ' ተብለው ከመኪና እንዲወርዱ ከተደረጉ በኋላ በአሰቃቂ ሁኔታ መረሸናቸው ታወቀ
(መሠረት ሚድያ)- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ ኢሰብአዊ እና ዘግናኝ ድርጊት መፈጸሙ ተሰምቷል።
ተመስገን ጌታቸው፣ ይታገሱ አሰግደው እና ግዛው ግርማዬ የተባሉ ሶስት የአማራ ክልል ተወላጆች ከተሳፈሩበት የሕዝብ ማጓጓዣ መኪና ላይ “ፋኖ ናችሁ” በሚል ውንጀላ ተገደው እንዲወርዱ ከተደረጉ በኋላ በግፍ መገደላቸውን የአካባቢው ምንጮች ለመሠረት ሚድያ ተናግረዋል።
ድርጊቱ የተፈጸመው አገና በተባለችው ልዩ ቦታ ሲሆን ወንጀሉን የፈጸሙት የመንግስት ኃይሎች ከአካባቢው የአበሽጌ አገና ፖሊስ እና ሚሊሻ አባላት ጋር በመተባበር እንደሆነ ተጠቅሷል።
ንጹሐኑ ዜጎች ከተሳፈሩበት መኪና ከወረዱ በኋላ እጃቸውን ወደኋላ በገመድ በማሰር አሰቃቂ እንግልት እንደፈጸሙባቸው እና በመጨረሻም ጭንቅላታቸውን በጥይት በመምታት በግፍ እንደረሸኗቸው ታውቋል።
የግፉ አፈጻጸም በዚህ ብቻ አላበቃም።
"ገዳዮቹ የሟቾቹን አስከሬን ወደ ትውልድ ቀያቸው ናቻ ቀሊት ቀበሌ ወስደው በመጣል ማንም ሰው አስከሬናቸውን እንዳያነሳና እንዳይቀብር ጥብቅ ክልከላ ጥለው ነበር" ብለው ለሚድያችን ቃላቸውን የሰጡት አንድ የአካባቢው ነዋሪ ናቸው።
"በዚህም ምክንያት የተገደሉት ሰዎች እጃቸው እንኳን ሳይፈታ ለሦስት ሙሉ ቀናት ክፍት ቦታ ላይ ተጥለው በእንስሳ እንዲበሉ እዛው እንዲቆዩ ተደርጓል" በማለት ሁኔታውን አስረድተዋል።
አስከሬኖቹ በተለይም ጭንቅላታቸው አካባቢ በተመቱበት የጥይት ምት ምክንያት ሙሉ በሙሉ በመጎዳቱ ገጽታቸውን ለማየት እና ለመለየት ጭምር የሚያስቸግር እና አሰቃቂ እንደነበር ተሰምቷል።
በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የመድረክ ውይይቶችና የምክክር ሂደቶች ስለ ሰላም ቢወራም ከጀርባ ግን የዜጎች ህይወት በዚህ መልኩ በስውር ማለቁና ኢሰብአዊ ጥቃት መፈጸሙ ማህበረሰቡን ለከፍተኛ ሀዘንና ስጋት ዳርጎታል።
| መሠረት ሚድያ |



