"በህይወት ያሉትን የማህበራችንን አባል ልንቀብር ሄድን!"
(መሠረት ሚድያ)- የኢትዮጵያ ፌዴራል ጠበቆች ማህበር ባልደረቦቹ በህይወት እያሉ አርፈዋል በሚል በተሳሳተ መረጃ ተገኝተው የቀብር ሥነ-ሥርዓት ላይ በመገኘታቸው ከፍተኛ ይቅርታ ጠይቋል።
በማህበሩ ይፋዊ መግለጫ መሰረት ለዚህ መንስኤ የሆነው አባል የሆኑት ጠበቃ ወይዘሮ አስቴር አርአያ አርፈዋል የሚል የሀሰት ሪፖርት ለማህበሩ መድረሱ ነው።
ይህንን መረጃ እውነት ነው ብሎ የተቀበለው ማህበሩ መጀመሪያ በቴሌግራም ገጹ ላይ የሀዘን መግለጫ ያወጣ ሲሆን በመቀጠልም የማህበሩ አመራሮች፣ ሰራተኞች እና ሌሎች አባላት በሙሉ በተባለው የቀብር ሥነ-ሥርዓት ላይ ተገኝተዋል።
ይሁን እንጂ የቀብር ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ከተገኙ በኋላ ነው አስደንጋጩ እውነታ የታወቀው።
በማህበሩ አባላት በተገኙበት ሲቀበሩ የነበሩት ግለሰብ ወይዘሮ አስቴር አሸብር የተባሉ ሌላ ሰው መሆናቸውንና የማህበሩ አባል የሆነችው ጠበቃ አስቴር አርአያ ግን በህይወት መኖሯን ማህበሩ አረጋግጧል።
"በህይወት ያሉትን የማህበራችንን አባል ልንቀብር ሄድን፣ ሌላ ሰው ሆነው በመገኘታችን እጅግ ተደናገጥን። ከዛ በኋላ ነው ስንደዋወል ስህተት እንዳለ የገባን። እጅግ ግራ የሚያጋባ ነገር ነበር" በማለት አንድ በስፍራው የነበሩ ጠበቃ ለሚድያን ተናግረዋል።
ማህበሩ በፈጠረው ስህተት ከፍተኛ ድንጋጤ ውስጥ መሆኑን በመግለጽ ለጠበቃ አስቴር አርአያ፣ ለቤተሰቦቻቸው እና ለማህበሩ አባላት በሙሉ ልባዊ ይቅርታ አቅርቧል።
በተጨማሪም በቴሌግራም ገጹ ላይ ተሰራጭቶ የነበረውን የተሳሳተ የሀዘን መግለጫ ወዲያውኑ ያነሳ ሲሆን ወደፊት እንዲህ ያሉ አስገራሚና አሳፋሪ ስህተቶች እንዳይደገሙ የውስጥ አሰራሩን በጥብቅ እንደሚገመግም ቃል ገብቷል።
| መሠረት ሚድያ |


