በኢትዮጵያ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አማኞች ግድያና ሁለንተናዊ ግፍ ለምን ሊቆም እንደማይችል ጠቋሚ መረጃዎች
በዶ/ር ተመስገን አለሙ ለመሠረት ሚድያ
(መሠረት ሚድያ)- በአማርኛ ሥነ-ቃል ውስጥ "የጠፋን ነገር ከሌባ ጋር ከፈለግኸው ፍጹም አታገኘውም" የሚባል የተለመደ አለ። በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በተለይም በኦሮሚያ ክልል አርሲ፣ ሸዋና ወለጋ፣ እንዲሁም በተለያዩ የታችኛው መዋቅሮች በኦርቶዶክስ አማኞች ላይ እየተፈጸመ ያለውን አሰቃቂና ስልታዊ ግድያ፣ መፈናቀልና አጠቃላይ ነባራዊ ሁኔታ ከዚህ በላይ በትክክልና በተጨባጭ ሊገልጽ የሚችል ብሂል የለም።
የአሁኑ ሥርዓት በሥልጣን መንበሩ ላይ እስካለ ድረስ ዓመታት ቢቆጠሩም በአገሪቱ ውስጥ ያለው አጠቃላይ የጸጥታ ቀውስና በኦርቶዶክስ አማኞች ላይ የሚፈጸመው ስልታዊ ማጽዳት (systematic persecution) እንደሚቀጥል በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ይህን የጨለምተኝነት (pessimism) ወይም ክፉን የመመኘት ውጤት ሳይሆን መሬት ላይ የሚታዩ ፖለቲካዊ፣ መዋቅራዊና ማህበራዊ እውነታ በምክንያታዊነት የመተንተን ጉዳይ ነው።
ሺ ጊዜ ተደጋግሞ ቢከሰትም የማያበራው የሰቆቃ እውነታ ልክ የዛሬ አሥር ዓመትም በተመሳሳይ ለአንድ ሳምንት ያህል እንደማኅበረሰብ አልቅሰን እንደምናልፈው ጥርጥር የለውም። ይህን እውነት በድፍረት ተጋፍጦ ስር ነቀል መፍትሔ ማሰብ ካልተቻለ ልክ እንደተለመደው ለአንድ ሳምንት አልቅሰንና አዝነን ወደ ኋላ የምንረሳው ወቅታዊ ክስተት ብቻ ሆኖ ይቀጥላል።
በእርግጥ ወደፊት የጊዜ ሂደት የሚያመጣው ለውጥ ሊኖር ይችላል፤ ነገር ግን ይህ ለውጥ የመሻሻል፣ የእኩልነትና የፍትሕ ሳይሆን፣ ዛሬ በዳር አገርና በገጠር ቀበሌዎች የሚፈጸመው ግድያና ማፈናቀል ወደ አዲስ አበባ እና ወደ ሌላው መሀል አገር በስፋት የሚሰፋፋ መሆኑ ብቻ ነው። ምክንያቱም ጥቃቱን በዘላቂነት የሚገታ አንዳችም መዋቅራዊ ሥራ በአሁኑ ሰዓት እየተሠራ ወይም እየታሰበ አይደለም። ለአሁኑ ሁለንተናዊ ሰቆቃና ግድያ በዚህ መልኩ እንደሚቀጥል የሚያሳዩ ስምንት መሠረታዊና ሰፊ ምክንያቶችን እንደሚከተለው በዝርዝር መተንተን ይቻላል።
1. የመንግሥት የርዕዮተ-ዓለም መነጽርና ታሪካዊ መስተጋብር (Ideological Threat)
የመጀመሪያውና መሠረታዊው ምክንያት አሁን ያለው የፖለቲካ ሥርዓትና በሥልጣን ላይ ያሉ ከፍተኛ አመራሮች የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ታሪካዊ ሚና፣ አስተዋጽኦና ምዕመናንን የሚያዩበት የርዕዮተ-ዓለም መነጽር ነው። የአሁኑ መንግሥት ድህነትን፣ ኋላ ቀርነትንና የትናንት ታሪክን ተያያዥ አድርጎ በሚስለው ትረካ ውስጥ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን እንደ ዋና ተዋናይ አድርጎ ይፈርጃል። ችግርን፣ ድህነትንና ማንኛውንም ከኋላ ቀርነት ጋር የተያያዘ ነው ብሎ የሚያስበውን ሁሉ ቢቻል በአንድ ጊዜ፣ ካልሆነም በጊዜ ሂደት እንዲጠፋና እንዲከስም ይፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን እንደ ድህነት ዘበኛ ስለሚቆጥር እንደ ትልቅ እንቅፋት ያያታል።
ይህ አስተሳሰብ በይስሙላ የሚነገር ሳይሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው በጻፉት "መደመር" መጽሐፍ ላይ በግልጽ ተቀምጦ ይገኛል። በመጽሐፉ ውስጥ ለአገር ዕድገትና ለብልጽግና አስተሳሰብ የሚመቸው የፕሮቴስታንት የሥራ ሥነ-ምግባር (Protestant Work Ethic) እንደሆነና የኦርቶዶክስ አስተሳሰብ ግን ከዚህ ጋር እንደማይገጥም ስልታዊ በሆነ መንገድ ተቀምጧል። ይህ የርዕዮተ-ዓለም አቋም ወደ መንግሥት የቢሮክራሲና አስተዳደራዊ የመንግሥት መዋቅር ሲወርድ ምዕመኑን ከሃይማኖቱ የመነጠልና የማዳከም ትልቅ ፕሮጀክት ሆኖ እንዲቀረጽ አድርጎታል።
ይህ የርዕዮተ-ዓለም አቋም ወደ ታችኛው የመንግሥት መዋቅር ሲወርድ ምዕመኑን በአንድም በሌላም መንገድ ጫና በማሳደር ከሃይማኖቱ የመንጠልና የማዳከም ትልቅ ፕሮጀክት ሆኖ እንዲቀረጽ አድርጎታል።
ጫናው የሚፈጸመው በሁለት መንገድ ነው፦ በአንድ በኩል የሥራና መሰል ማበረታቻ ዕድሎችን በሃይማኖት ስብጥር ላይ በመመስረት ለተወሰኑ ወገኖች ብቻ በልዩነት በመስጠት ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የቤተክርስቲያኗን አስተምህሮ "የጠንቋይና የደብተራ ሥርዓት"፣ የመንግሥት "ነቢያት ሲሰባበሩ ያዩት ትልቅ ዓለት" ወይም "የሰሜን ዛር ሃይማኖት" እያሉ ካለ ምንም ተጠያቂነት በአደባባይ በማዋረድ (humiliate በማድረግ) ምዕመኑን ማሸማቀቅ ነው።
አሁን አሁን በፌደራል መሥሪያ ቤትም ሆነ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ኦርቶዶክስ ሆኖ የመንግሥት ሥራ ማግኘት፣ በተለይም የኃላፊነት ቦታ መውሰድ በአፓርታይድ ደቡብ አፍሪካ ጥቁር ሆኖ የመሾምን ያህል አስገራሚ እየሆነ ነው። የቤተክርስቲያን ባንዲራና አርማ ይዘህ ስለወጣህ ተብሎ በፀጥታ ኃይሎች የሚገደልበትንም ጊዜ አይተናል። "መልካም ወጣት" በሚሉ መንግሥታዊ ከለላ ባላቸውና የገንዘብ ድጋፍ በሚደረግላቸው መርሐ-ግብሮች የኦርቶዶክስ ወጣቶችን "ከጨለማው ቦታ እንኳን ወደ ብርሃኑ መጣችሁ" እያሉ በአደባባይ መስበክና ማንኳሰስ የተለመደ ሆኗል። ስለዚህ በአጠቃላይ ይህ አሁን የምናየው ግድያ ከመንግሥት ከቆመበት የአስተሳሰብ ዓምድ ስለሚነሳ ሊቆም አይችልም።
2. የጠቅላይ ሚኒስትሩ የ"ብልጽግና ወንጌል" ዕይታና ሃይማኖታዊ ፋታሊዝም (Prosperitarian Fatalism)
ሁለተኛውና እጅግ አደገኛው ምክንያት በጠቅላይ ሚኒስትሩና በዙሪያቸው ባሉ አጋሮቻቸው ዘንድ የሚነገረው "የብልጽግና ወንጌል" (Prosperity Gospel) ዓለም አቀፋዊ ዕይታ ነው። በዚህ ፍልስፍና መሠረት አንድ ሰው ሁልጊዜ "በጎ ተስፋ ሊኖረው፣ ብሩህና ትክክለኛ ስሜት ሊሰማው" ይገባል። በመሆኑም መከራና ሥቃይ ምንም ያህል ቢበዛ እንደ አጀንዳ መታየት የለበትም። ከዚህ አስተሳሰብ በመነሳትም 'አትግደሉን' ብሎ መጮኽ በራሱ እንደ ወንጀል ይቆጠራል። ሰዎችን ከሞት ማዳን የመንግሥት ቀዳሚ ኃላፊነት ቢሆንም ይህንን ሳያደርግ ሲቀር ግን ተጠያቂነት ከመምጣት ይልቅ፣ 'አትግደሉን' ማለት ጥፋት ሆኗል። በዚህ የተዛባ ዕይታ ምክንያት በአገሪቱ ውስጥ የሚከሰቱ ማናቸውም ዓይነት እልቂቶችና ሰቆቃዎች ወይ እንደሌሉ ተደርገው ይቆጠራሉ፣ ወይም "በፈጣሪ የተፈቀዱና የተወሰኑ" (ordained by God) ተደርገው ይታለፋሉ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ይህንን አቋማቸውን በአደባባይ ለመናገር አፍረው አያውቁም። በብዙ መድረኮች ላይ በርሃብ ሆዳቸው ባዶ ሆኖ የሚያድሩ ምስኪን ኢትዮጵያውያንን ሳይቀር "ዓይናችሁ የታወረ፣ የምናደርገውን ተአምራዊ የኢትዮጵያ ብልጽግና ማየት የተሳናችሁ" እያሉ በይፋ ከስሰዋል። በአካባቢያችሁ ያለውን ሰላም ማስከበር የእኔ ኃላፊነት አይደለም፤ እኔ በአካባቢዬ (አራት ኪሎ ማለታቸው ነው) ከጎረቤቶቼ ጋር በሰላም ነው የምኖረው' በማለት በሚሊዮኖች በሚቆጠሩ ሕዝቦች ሥቃይና ሰቆቃ ላይ አላግጠዋል። ይህ ማለት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ንጹሐን ኦርቶዶክሳውያንና ሌሎች ዜጎች ቢያልቁም፣ በመንግሥት ዘንድ አንዳችም የሐዘኔታ፣ የጭንቀት ወይም የጸጸት ስሜት አይፈጥሩም።
ይህን አሰቃቂ እውነታ ይበልጥ አደገኛ የሚያደርገው የውስጥ ሃይማኖታዊ አተረጓጎማቸው ነው። በጥንታዊው የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ትረካዎች ውስጥ ያሉትን ሃሳቦች በተዛባ መንገድ በመውሰድ፣ አሁን የምናየውን መከራና ሥቃይ "አገሪቱ ለዘመናት ያከማቸችውን የጋራ ኃጢአት ለማንጻት የሚደረግ ሂደት(ስርየት" አድርገው ይረዱታል። "የፈጣሪ ምሕረት የሚመጣው በደም ነው" የሚል እጅግ አደገኛና ጨካኝ ሃይማኖታዊ እምነት ስላላቸው፣ በደልና ግድያው ሲፈጸም እንደ ተፈጥሮአዊ የጽዳት ሂደት ስለሚቆጥሩት ጥቃቱን ለማስቆም አንዳችም ፖለቲካዊ ፍላጎት የላቸውም።
3. የተጠያቂነት አለመኖርና የውስጥ ሰዎችን በመጠቀም የሚደረግ የገጽታ ግንባታ (Systematic Impunity & Co-opted Cover-up)
ሦስተኛው ምክንያት በቤተክርስቲያኗና በምዕመኑ ላይ በደል፣ ግድያና ሥቃይ በሚፈጽሙ አካላት ላይ መንግሥት ተጠያቂነትን የማሥፈን ፍላጎት የሌለው መሆኑ ነው። ከላይ እንደተገለጸው መንግሥት በፖሊሲ ደረጃ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የብልጽግና እንቅፋት ነች ብሎ ስለሚያምን፣ እንደ አርሲው ዓይነት አሰቃቂና ሰቅጣጭ ወንጀል ሲፈጸም በሕግ አግባብ የወንጀል ፈጻሚዎችን ከመቅጣት ይልቅ ለፈጻሚዎቹ ከለላና ሽፋን ይሰጣል። ለዚህ የሽፋን ስራ ደግሞ የራሳቸውን የኦርቶዶክስ ታሪክና የሃይማኖት ሰውነት ያላቸውን ግለሰቦችና ተቋማት እንደ ጭምብል (ፊት መሸፈኛ) ይጠቀማል።
ለዚህ ትልቁ ማሳያ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ የሆኑት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ናቸው። እኚህ ግለሰብ ዛሬ እንዲህ የመንግሥት ባለሟል (ባለሥልጣን) ሳይሆኑ የነበራቸውን የኦርቶዶክስ እውቅናና ማህበራዊ ተቀባይነት በመጠቀም ፀረ-ኦርቶዶክስ ለሆነው የመንግሥት መዋቅር የገጽታ ግንባታና ማስተባበያ ያቀርባሉ። በክርስቲያኖቹ ላይ የሚፈጸመውን ስልታዊ ግድያ "በጽንፈኞች የተደራጀና ከውጭ የመጣ አጀንዳ" አድርጎ በማቅረብ የመንግሥትን ቀጥተኛ መዋቅራዊ እጅ ይሸፍናሉ።
አሁን የሚታየውን ውድቀት በሙሉ ዳንኤል ክብረት 'ያለፈው በሕወሐት የሚመራው መንግሥት የተከለው የመርዝ ዛፍ ፍሬ' እያሉ ያስተባብላሉ:። ነገር ግን ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆኑ አብዛኛዎቹ የካቢኔ አባላቱ ራሳቸው የዚያው ሥርዓት ውጤት፣ አራማጅና ፈጻሚዎች የነበሩ መሆናቸው የትላንት ትዝታ ለሆነው መከረኛው ሕዝብ ከንቀትና ምን ታመጣላችሁ ዕብሪት የበለጠ መልእክት አይሰጠውም።
4. የሃይማኖት መሪዎችን ማዳከም፣ መጥለፍና መተካት (Subversive Infiltration of Leadership)
አራተኛው ምክንያት ለኦርቶዶክስ ሃይማኖት ሕዝቡን በአባታዊ አንድነት አንድ አድርገው ለማንቀሳቀስ፣ መብቱን ለማስከበርና ድምፅ ለመሆን የሚችሉ ብቁ መሪዎች እንዳይኖሩ ሆን ተብሎ የተሠራው የውስጥ ማዳከም ሥራ ነው። በአሁኑ ሰዓት ቅዱስ ሲኖዶሱም ሆነ ሌሎች የሃይማኖት አባቶች፣ ምዕመኑን እረኛ የሌለው መንጋ አድርገውታል። እንደ ድሮው ለሕዝብና ለሃይማኖቱ እውነት ፊት ለፊት ቆሞ የሚጋፈጥ መሪ ማግኘት አስቸጋሪ የሆነው መንግሥት በሃይማኖት አባቶች ላይ በሚያደርገው የተራቀቀ ጥቅማጥቅም፣ ሥጋዊ ማስፈራሪያና የመጥለፍ (co-optation) ስትራቴጂ ነው።
እዚህ ላይ ከሁለት ዓመት በፊት (በ2015 ዓ.ም.) ሕገ-ወጥ የኦሮሚያ ሲኖዶስ ለመመስረት የተሞከረበትንና በመንግሥት ኃይሎች በግልጽ ይደገፍ የነበረውን እንቅስቃሴ ማስታወስ ይገባል። በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲኖዶሱን ለመክፈል የሚደረገውን ጥረት የሚቃወሙትን አካላት በግልጽ ቴሌቪዥን ላይ ወጥተው አስፈራርተው ነበር። ዓላማው ሕዝቡን መከፋፈልና ማሸበር የነበረ ቢሆንም፣ ምዕመኑን ግን በአንድነት በነቂስ ወጥቶ አቋሙን ሲያሳይ መንግሥት ወደ ኋላ ያፈገፈገ አስመስሎ ነበር። ሆኖም፣ መንግሥት ያንን አጋጣሚ የተጠቀመው ሕዝቡን ሊያንቀሳቅሱና ሊያስተባብሩ የሚችሉ ጠንካራና ተጽዕኖ ፈጣሪ አባቶችን (Galvanizing Figures) ለይቶ ለማወቅ ነበር።
በመቀጠልም የመንግሥትን የማስገደጃ ኃይል (coercive power) በመጠቀም (አንዳንዶቹን ወደ አገር እንዳይገቡ በማገድ) እንደ ዳንኤል ክብረት ያሉ ሰዎችን መሣሪያ በማድረግ፣ እነዚያን ጠንካራ አባቶች በማግለልና በማጥፋት በራሱ ቁጥጥር ሥር ባሉና ለሥጋቸው በቆሙ ታማኝ ሰዎች ተክቷቸዋል። ይህም ተቋሙን መሪ አልባ የማድረግና በዚህም መንጋውን አንድ በአንድ ከሃይማኖቱ የመንጠል ተኩላዊ ፕሮጀክት አካል ነው።
5. ቤተክርስቲያንን እንደ ሥልጣንና ፖለቲካ ስጋት መቁጠር (The Myth of Domination)
አምስተኛው ምክንያት፣ መንግሥት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ሰፊ የሕዝብ መሠረትና ታሪካዊ አንድነትን የመጠበቅ አቅም ለሥልጣኔ ዋነኛ ስጋት ናት ብሎ ማመኑ ነው። ቤተክርስቲያኗ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ምዕመናንን በአንድ አገራዊና ሃይማኖታዊ ጥላ ሥር ማሰባሰብ መቻሏ፣ የራሱን ከፋፋይ የብሔር ፖለቲካ ለማስቀጠል ለሚፈልገው ገዥ አካል እንደ ትልቅ አደጋ ይታያል።
ሕዝቡን በዘርና በጎሳ ከፋፍሎ ለመግዛት፣ ይህን አገራዊ ትሥሥር የያዘውን ተቋም ማዳከም፣ ምዕመኑን ማሸበርና በነዋሪነቱ ላይ ዋስትና ማሳጣት የመንግሥት ስውር ስትራቴጂ በመሆኑ ግድያው እንዲቀጥል ይደረጋል። መንግሥት ቤተክርስቲያኗን “የቀድሞው ሥርዓት ናፋቂ” ወይም “ለብሔር መብት ዕድገት እንቅፋት” አድርጎ በመሳል፣ የራሱን የሥልጣን ዕድሜ ለማራዘም ሲል የጥላቻ ፖለቲካ መጋቢ ያደርጋታል።
6. የሕዝብ ስብጥር ለውጥና ተቃውሞን የመለየት ሴራ (Demographic Engineering & Tactical Provocation)
ስድስተኛው ምክንያት፣ በተለይም በኦሮሚያ ክልልና በአዲስ አበባ ዙሪያ የታቀደ የሕዝብ ስብጥር ለውጥ (Demographic Engineering) ለማድረግ የሚሠራው ስልታዊ ሴራ ነው። የኦርቶዶክስ አማኞችን ከቀዬአቸው ማፈናቀል፣ አብያተ ክርስቲያናትን ማፍረስ፣ ንብረታቸውን ማውደም እና በግልጽ መግደል አማኙ ማኅበረሰብ አካባቢውን ለቆ እንዲሰደድ ያደርገዋል።ይህም ኦርቶዶክስ ሃይማኖትን የአንድ ብሔር ሃይማኖት አድርጎ በመሳል፣ ለምሳሌ ኦሮሞ ሆኖ ኦርቶዶክስ መሆንን እንደ ነውር በማስመሰል የሚፈጸም፣ በቀጣይም በሃይማኖትና በብሔር አንድ ወጥ የሆነ ክልል የመፍጠር ፍላጎት የፈጠረው ነው።
ከዚህም በተጨማሪ፣ እነዚህ ጥቃቶችና በአደባባይ የሚሰነዘሩ ሰብአዊነትን የሚያዋርዱ ስድቦች ምዕመኑን ሆን ብሎ ለማስቆጣትና ለማነሳሳት (provoke ለማድረግ) ጥቅም ላይ ይውላሉ። ዓላማው ወደፊት ተቃውሞ ሊያስነሱ የሚችሉ ኃይሎችንና የውስጥ የመቋቋም ምንጮችን ቀድሞ ለይቶ ማወቅና እነሱን በተናጠል ማጥፋት (eliminate ማድረግ) ነው። ይህ ስልታዊ ሴራ ያሰቡትን የሕዝብ ስብጥር የበላይነት በየአካባቢው ለመፍጠርና መሬት ለመቀማት ሆን ተብሎ የሚደረግ በመሆኑ፣ ግድያው ዓላማውን እስካላሳካ ድረስ ሊቆም አይችልም።
7. የሕግ የበላይነት መፍረስና የጽንፈኛ ኃይሎች ከመንግሥት ጋር መወራረስ (Institutionalized Extremism)
ሰባተኛው ምክንያት፣ በአገሪቱ ውስጥ የሕግ የበላይነት ሙሉ በሙሉ መክሰሙና በየክልሉ ያሉ ጽንፈኛ መዋቅሮች ከመንግሥት የጸጥታ አካላት ጋር ያላቸው ጥብቅ ቁርኝት ነው። በአርሲም ሆነ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች የሚፈጸሙ ማንንትን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች፣ ግድያዎችና መፈናቀሎች እንዲሁ በድንገት የሚከሰቱ ሳይሆኑ፣ በየክልሉ ያሉ ጽንፈኛ ኃይሎች ከመንግሥት የጸጥታ መዋቅር ጋር ያላቸው ጥብቅና የተቀናጀ ቁርኝት ውጤቶች ናቸው።
ይህ ዓይነቱ ክስተት በፖለቲካ ሳይንስ “የመንግሥት መዋቅር በጽንፈኞች መታገት” (State Capture) የሚባል ሲሆን፣ የታጠቁ ቡድኖችና ከመንግሥት ባለሥልጣናት እንዲሁም ከክልል የጸጥታ ኃይሎች ጋር የሚደረግን ስልታዊና ቀጥተኛ ትብብር ያመለክታል። በጥቃቶች ወቅት መደበኛው የመከላከያ ኃይልም ሆነ ፖሊስ ሆን ብሎ ዘግይቶ መድረሱ፣ አልፎ ተርፎም ጥቃቱን እያየ እንዳላየ ማለፉ፣ ወንጀለኞቹና አስፈጻሚዎቹ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ለመሆናቸው ማረጋገጫ ነው። ይህ መወራረስ (Symbiotic Relationship) የኢትዮጵያን የጸጥታ ተቋማት ገለልተኝነት ሙሉ በሙሉ ያጠፋቸው ሲሆን፣ የመንግሥት የኃይል መዋቅር ራሱ የወንጀሉ ተባባሪና ቀጥተኛ ፈጻሚ እንዲሆን አድርጎታል። በሕዝብ ግብር የሚተዳደሩ ተቋማት የጽንፈኝነት መፈልፈያና መጠበቂያ በሆኑበት ነባራዊ ሁኔታ፣ ከእነዚሁ አካላት ሰላምን፣ እኩልነትንና ፍትሕን መጠበቅ ፍጹም የማይቻል የፖለቲካ የዋህነት (Political Naivety) ነው።
8. የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ስልታዊ ዝምታና ግድየለሽነት (Global Blindspot)
ስምንተኛውና የመጨረሻው ምክንያት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳውያን ላይ እየደረሰ ያለው የዘር ማጥፋትና የሃይማኖት ማፅዳት ወንጀል ትኩረት አለማግኘቱ ነው። መንግሥት ይህን ጥቃት በዓለም አቀፍ መድረክ እንደ ተራ "የጎሳ ግጭት"፣ "የአየር ንብረት ለውጥ ያመጣው የሀብት እጥረት ግጭት" ወይም "የዳር ድንበር ይገባኛል ጥያቄ" አድርጎ በማቅረብ እውነተኛውን ገጽታ ይሸፍናል።
ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችና መንግሥታትም በጂኦፖለቲካዊ ጥቅሞችና በዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች ምክንያት በጉዳዩ ላይ ጠንካራ ጫና ማሳደር አልፈለጉም። ይህ ስልታዊ ዝምታ ደግሞ የአሁኑ ሥርዓት ካለ ምንም ስጋትና ተጠያቂነት በኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ላይ የሚፈጸመውንና የሚያስፈጽመውን ግፍ በነፃነት እንዲቀጥልበትና ይበልጥ እንዲደፋፈር በር ከፍቶለታል።
መውጫ መንገዱና የመንግሥት ወጥመድ (Armed Struggle vs. Popular Resistance)
ከላይ የተዘረዘሩት መዋቅራዊ በደሎችና ቀጣይነት ያላቸው ጥቃቶች ብዙዎቹን የኦርቶዶክስ አማኞች ወደ ተስፋ መቁረጥና የመጨረሻ አማራጭ ወደሆነው የትጥቅ ትግል (armed struggle) እንዲያዘነብሉ እያደረጋቸው ይገኛል። ሆኖም ግን፣ ወደ ትጥቅ ትግል መግባት መንግሥት ሆን ብሎ ያዘጋጀው ወጥመድ ውስጥ (trap) ቀጥታ መግባት መሆኑን በጥልቀት መረዳት ያስፈልጋል። ይህ እርምጃ ለመንግሥት ፍጹም ምቹ የሆነ ሰበብ (pretext) በመስጠት፣ የኦርቶዶክስ ተከታዮችን በሙሉ "የሃይማኖት ጽንፈኞችና አሸባሪዎች" በሚል ስም በዓለም አቀፍና በአገር ውስጥ መድረክ ፈርጆ በነፃነት እንዲጨፈጭፍና እንዲያሳድድ በር ይከፍትለታል።
የጠቅላይ ሚኒስትሩን ታሪካዊ ንግግሮችና ማስፈራሪያዎች ማስታወስ ለዚህ በቂ ማሳያ ነው። ገዥው አካል የማስገደጃ ኃይሉን ከመጠቀሙ በፊት፣ የቤተክርስቲያኗን አባቶች (ሊቃነ ጳጳሳትን) ሰብስቦ የትዕግሥታቸውንና የአቅማቸውን ልክ ለመለካት በይፋ ዝቶባቸዋል። በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በግልጽ እንደተናገሩት፣ ማንኛውም ዓይነት ጠንካራ ተቃውሞ ከመንግሥት ዘንድ የሚያጋጥመው የጭፍጨፋና የኃይል እርምጃ፣ በደርግ ዘመን የነበረውን የኢሕአፓ (EPRP) የነጭና ቀይ ሽብር እልቂት የሚያስንቅ እንደሚሆን ገልጸው ነበር።
ስለዚህ፣ የኦርቶዶክስ ምዕመናን አሁን ባለው ሁኔታ በስሜት ተገፋፍተው ወደ ትጥቅ ግጭት የሚገቡ ከሆነ፣ መንግሥት ይህንን አጋጣሚ ተጠቅሞ ከፖለቲካ ጋር አንዳችም ንክኪ የሌላቸውን ንጹሐን አማኞችን ጭምብል በለበሰ ሕጋዊ መንገድ እስከመጨረሻው ያጠፋቸዋል።
ስለሆነም መንግሥትን ለመጋፈጥ መዋቀር ያለበት ስልት የትጥቅ ትግል ሳይሆን ሁለንተናዊ የሕዝብ ተቃውሞና ሕዝባዊ እምቢተኝነት ነው። አሁን ያለው ሥርዓት ከታጠቀ ኃይል ይልቅ ሕዝባዊ እምቢተኝነትንና ሰላማዊ ሰልፎችን በእጅጉ ይፈራል። ምክንያቱም መንግሥት የመግደልና የማጥፋት ከፍተኛ ዝንባሌ ስላለው፣ የታጠቀ ኃይል ሲገጥመው ወንጀሉን የሚያስተባብልበት "የአገር ደህንነት" እና "ከታጣቂ ጋር መዋጋት" የሚል ዐውዳዊ ሰበብ ያገኛል፤ በሰላማዊ የሕዝብ እምቢተኝነትና አልገዛም ባይነት ውስጥ ግን ይህንን ሰበብ ማግኘት አይችልም።
በዚህ የታሪክ አጋጣሚ ውስጥ ትልቁን ድርሻ መውሰድ ያለባቸው በመንግሥት የጸጥታ መዋቅር፣ በወታደራዊና በደህንነት ተቋማት ውስጥ ያሉ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ናቸው። እነዚህ ወገኖች ማስተዋል ያለባቸው ትልቅ እውነት አለ፦ የምታገለግሏትና የምትጠብቋት ቤተክርስቲያን ሙሉ በሙሉ ከፈረሰችና ከጠፋች፣ ወደፊት የምትጠብቋት አገር የምትባል አንዳችም ምድር አትኖርም። ዛሬ ሥርዓቱን ለማስቀጠል የምትሰጡት ጥበቃና የምትፈጽሙት ትዕዛዝ፣ ነገ ተራው ደርሶ በተናጠል (individually) የእናንተንና የቤተሰባችሁን ሕልውና እንደሚያጠፋ መገንዘብ ይገባል።
ማጠቃለያ
በአጠቃላይ እነዚህ 8 ምክንያቶች ፍንትው አድርገው የሚያሳዩት በኢትዮጵያ በኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለው ሁለንተናዊ ግፍና ስልታዊ ግድያ እንዲሁ በአጋጣሚ የሚከሰት ሳይሆን፣ ጥንቁቅ በሆነ የመንግሥት የብልጽግና ርዕዮተ-ዓለም፣ በሃይማኖታዊ ሰበብ፣ የውስጥ ሰዎችን በመጠቀም በሚደረግ የገጽታ ግንባታ ፣ እና ተቃውሞን ለይቶ በማጥፋት ስትራቴጂ ላይ የተመሠረተ መሆኑን ነው።
በደሉን የሚፈጽመውና ለፈጻሚዎቹ ከለላ የሚሰጠው ኃይል ራሱ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ተሸሽጎ እስካለ ድረስ፣ ከዚሁ ሥርዓት ፍትሕንና ሰላምን መጠበቅ ፍጹም የማይቻል ነው። ስለዚህ፣ መፍትሔው በመንግሥት ወጥመድ (በታጠቀ ግጭት) ውስጥ ሳይገቡ፣ መላው ምዕመን፣ የጸጥታ ኃይሎችና የተቋሙ መዋቅሮች በአንድነት ቆመው በሰላማዊ፣ ሥልታዊና በተቀናጀ የሕዝብ እምቢተኝነት መብታቸውንና የቤተክርስቲያናቸውን ሕልውና ማስከበር ብቻ ነው። ሕዝባዊ እምቢተኝነትን በአግባቡ መምራት የሚችል ኃይል፣ 'የትጥቅ ትግል ላድርግ' ቢል እንኳ ጠንካራ ተቋማዊ ቁመናና የሚያስችል አቅም ይፈጥርለታል።
***መሠረት ሚድያ ላይ የሚቀርቡ አስተያየቶች በሙሉ የፀሀፊዎቹ እንጂ የሚድያው አቋም እንዳልሆኑ ልናስታውስ እንወዳለን።
| መሠረት ሚድያ |



Well said.
መሰረት ሚዲያ ይሄ ልጥፉችሁ ህዝብን ወደ ግጭት የሚቀሰቅስ ነዉ